World News

Goolgule.com: የጄ/ል አበባው “ከፈለገ ይፈንዳ” ንግግር በትግራይ ሌላ ችግር እያፈነዳ ነው

Posted by: Berhane.Habtemariam59@web.de

Date: Wednesday, 03 July 2019

 
July 3, 2019 10:36 am
  • ትግራይን የተቆጣጠሩ የቀድሞ አገዛዝ ርዝራዦች አሁንም ለዐቢይ ችግር ናቸው

በባህርዳርና አዲስ አበባ በተቀናጀ መልኩ በተካሄደው የመፈንቅለ መስተዳድር/መንግሥት ህይወታቸውን ባጡት ጄ/ል ሰዓረ መኮንን አስከሬን ሽኝት ላይ በጄ/ል አበባው ታደሰ የተነገረው በትግራይ ሌላ ችግር እያፈነዳ መሆኑ ተሰማ። በአዲስ አበባ በቅድስት ሥላሴ ሊካሄድ ታቅዶ የነበረው የጄ/ል ሰዓረ ቀብር ትግራይ መደረጉ ይህንኑ ተከትሎ ለተነሳው “እሣት” ማዳፈኛ ይሆን ዘንድ ለፖለቲካ ፍጆታ የዋለ መሆኑ ተገለፀ። በአሜሪካ የውጭ ጉዳይ ሚ/ር መ/ቤት የአፍሪካ ጉዳዮች ኃላፊው ቲቦር ኒጌይ ትግራይ የመሸጉ የህወሓት ርዝራዦች አሁንም ለጠ/ሚ/ር ዐቢይ ችግር ፈጣሪዎች እንደሆኑ ተናገሩ።

ህወሓትን በአደባባይ እንደሚያገለግል እየተናገረ መከላከያውን በኤታማዦር ሥልጣን ለረጅም ዓመታት ሲመራ የነበረው ሳሞራ የኑስን በመተካት በለውጡ ማግስት በኤታማዦርነት የተሾሙት ሰዓረ መኮንን ገና ከጅምሩ በርካታ ስም ሲሰጣቸው መቆየቱ ይታወቃል። መደመራቸውና ለውጡን ለማስቀጠል በመወሰን ኢትዮጵያዊነታቸውን በገሃድ እየመሰከሩ መከላከያውን መምራት የጀመሩትን ሰዓረ በተደጋጋሚ “ከሃዲ” በመባል ፕሮፓጋንዳ ሲነዛባቸውና በትልልቆቹ የህወሓት ባለሥልጣናት ሳይቀር የትግራይ ጠላት ተደርገው ሲፈረጁ ቆይተዋል። ከዚህም ጋር ተያይዞ የትግራይ ተቆርቋሪ ነን በሚሉ የሰዓረ መኮንን ፎቶ በየቦታው ተዘቅዝቆ ሲሰቀል ነበር።

በሚያስገርም መገጣጠም የጄ/ል ሰዓረ ልጅ መዓሾ ሰዓረ በሽኝቱ ሥነሥርዓት ላይ የአባቱን አስከሬን እያየና ምንም ፅሁፍ ሳይዝ ራሱን መቆጣጠር አቅቶት አንገቱን እየደፋ ጥርሱን ነክሶ ስለ አባቱ የተናገረው ጥቂት ግን ትልቅ መልዕክት ያዘለ ነበር። “አባቴ በአንድነት፣ በመቻቻል፣ አብሮ በመሥራት የሚያምን ፍፁም ኢትዮጵያዊ ነበር። ጄ/ል ሰዓረ ስለሞተ አገር ይፈርሳል ማለት አይደለም፤ እኛ ተባብረን ከቆምን ኢትዮጵያን አንድ እናደርጋታለን” በማለት ነበር የአባቱን ኢትዮጵያዊነትና አንድነት ወዳጅነት በመጥቀስ ንግግሩን ያበቃው።

በመቀጠል ንግግር ያደረጉትና ቦምቡን ያፈነዱት ሌተና ጄ/ል አበባው ታደሰ ሲሆኑ እርሳቸውም “እዚህ ላይ አንድ ነገር ልንገራችሁ” በማለት ነበር ሳግ እየተናነቃቸው ጓደኛቸው የነገሯቸውን ይፋ ያደረጉት። አበባው ቀጠሉ “እዚህ ላይ አንድ ነገር ልንገራችሁ፤ ከፈለገ ይፈንዳ፤ ይሄ ለውጥ ከመጣ በኋላ ሰዓረ እንደ ከሃዲ ተቆጠረ፤ በጥቂት ቡድኖች፤ ኢትዮጵያዊነቱ አሳልፎ እንዲሰጥ ከፍተኛ ተፅዕኖ ደረሰበት። ‘አበባው እንደዚህ እያሉኝ ነው፤ ቤተሰቤ ይበተናል እንጂ ኢትዮጵያዊነቴን አሳልፌ አልሰጥም፤ ማንም ይምጣ ማን የእኔ መሪዬ ነው፤ አክብሬ እስክምሞት ድረስ በኢትዮጵያዊነቴ ሳልደራደር እሠራለሁ’ አለ” በማለት ጄ/ል አበባው ንግግራቸውን ከጄ/ል ሰዓረ ልጅ ንግግር ጋር አሳስመውታል።

ከመንግሥት መገናኛ ብዙሃን ተነግሮ የነበረው ጄ/ል ሰዓረ በአዲስ አበባ መንበረ ፀባዖት ቅድስት ሥላሴ እንደሚቀበሩ ነበር። ይህ ግን ተቀይሮ የሰዓረና የገዛዒ አስከሬን ወደ ትግራይ ተወስዶ በተወለዱበት ቦታ ይቀበራል ወደሚል ተቀየረ። ይህ በሆነበት ጊዜ ጄ/ል ሰዓረ የኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊትን ሲመሩ የነበረ እንደመሆኑ በክልል ሳይሆን አዲስ አበባ መቀበር አለባቸው ብለው በማኅበራዊ ሚዲያ (በተለይ ፌስቡክ) የተከራከሩ የትግራይ ተወላጆች ነበሩ። እነዚህን በመቃወም ቀብሩ ትግራይ መሆን አለበት ብለው የተሟገቱም ቁጥራቸው ጥቂት ልነበረም።

ሆኖም ግን የጄ/ል ሰዓረ ትግራይ መቀበር ያስፈለገበት ዋና ምክንያት የታወቀው ትግራይ ሥነሥርዓቱ በተካሄደ ጊዜ የህወሓት ሊቀመንበር ደብረፂዮን ገብረሚካኤል ንግግር ባደረገበት ወቅት ነበር። በለቅሶ ላይ እንዳለ ሐዘንተኛ፣ እንደተጎዳ ሰው፣ ወይም ጉዳቱ እንዳሳመመው ኢትዮጵያዊ ሳይሆን ደብረፂዮን በክልሉ ምክር ቤት ወይም በህወሓት ድርጅታዊ ስብሰባ ላይ የፖለቲካ ንግግር የሚያደርግ ይመስል በቀበር ሥርዓቱ ላይ ለተሰበሰበው ታዳሚ “እንደ ትግራይ የምንታገሰው ፅንፈኛ ሊኖር አይችልም” ብሏል።

ሲቀጥልም “ዴሞክራሲ እናስፋ በተባለበት አገርና ሕዝብ ይክሳሉ ተብለው ብዙዎች ተፈትተዋል፤ የነበረው ዴሞክራሲ ሊሰፋ ይቅርና አገራችን የጽንፈኞች ጸረ ሕዝቦችና ጸረ ሕገመንግሥት ኃይሎች መፈንጫ ሆናለች” በማለት ህወሓት በግፍ አስሯቸው የነበሩትን ሁሉ “በጽንፈኝነት” በመፈረጅ መፈታታቸውን አውግዟል። እንደነዚህ ዓይነት ሰዎች ከእስር በመፈታታቸውም “ሰላማችን ደፈረሰ፣ አገራችን የነውጥና ግድያ መዓከል ሆነች፤ የፖለቲካ አሰላለፉ ተዛብቷል ፤ ሁሉ ነገር ተደበላልቋል፤ ጉዳቱን ነጋ ጠባ እየቆጠርን፣ እየመዘገብን እንገኛለን፣ ትዕግስት በዝቷል፤ አሁን ውሳኔ የሚጠየቅበት ጊዜ ላይ ደርሰናል፤ ሕገወጥነት ነግሷል፤ እኛ በሰላም በውይይት ሕዝብ የሚወደውን ይምረጥ እንላለን፤ ትምክህተኞች ግን በግርግርና በግድያ ሥልጣን በጉልበት እንይዛለን እያሉ ነው። የትግል ስልታችንን ደግመን ልንፈትሽ ይገባናል፤ … አሁን ይበቃል ልንላቸው ይገባል” ባለበት ንግግሩ ትግራይ ሸምቀው የተቀመጡትን ወንጀለኞች አሳልፎ ባለመስጠት ሕገወጥነትን በማስፋፋት የርሱ ክልል ትግራይ ፊትአውራሪ መሆኑን የዘነጋው ይመስል ነበር።

“እዚህ ላይ አንድ ነገር ልንገራችሁ፤ ከፈለገ ይፈንዳ፤ ይሄ ለውጥ ከመጣ በኋላ ሰዓረ እንደ ከሃዲ ተቆጠረ፤ በጥቂት ቡድኖች፤ ኢትዮጵያዊነቱ አሳልፎ እንዲሰጥ ከፍተኛ ተፅዕኖ ደረሰበት።” ጄ/ል አበባው

ደብረፂዮን በዚህ ብቻ አላበቃም “እንደ ትግራይ የምንታገሰው ፅንፈኛ ሊኖር አይችልም … የግድያው ዓላማ የኢትዮጵያን ሕዝብ እርስበርሱ ማጋጨት የነበረ ሲሆን ከሌላ ተጨማሪ ጥፋት ለመዳን ሕዝብ ለሕገመንግሥቱ መከበር በ(ፌዴራሉ) አመራር ላይ ጫና ሊፈጥር ይገባዋል” በማለት ሕዝብ በፌዴራል ሥርዓቱ ላይ ኢ-ሕገመንግሥታዊ በሆነ መልኩ ሕዝብ እንዲነሳ “የክተት ጥሪ” በማቅረብ ህወሓት ከለወጡ መጀመር አንስቶ “ዐቢይ አህመድ አገር መምራት አልቻለም” የሚለውን ዲስኩር የሚደግፍለት ንግግር አድርጓል።   

ደብረፂዮን ይህንን መሰሉን ንግግር ያድርግ እንጂ ለፌዴራሉ ሥርዓት ባለመታዘዝ በወንጀል የተጠረጠሩ የቀድሞ የህወሓት ሹሞችን ደብቆ በመያዝ እርሱ የሚመራው ክልል ቀዳሚው መሆኑን የዘነጋው ይመስላል በማለት አስተያየት ሰጪዎች ይናገራሉ። ከመደበቅም አልፎ የፌዴራል ኃይል በሕግ ማዘዣ ፍርድቤት እንዲቀርቡ ጥሪ ሲያቀርብም አሻፈረን በማለት የሚታወቀውና “በፌዴራሉ ላይ ያበጠ ክልል” በመባል የሚጠራው እርሱ የሚጠራውና ለሕገመንግሥታዊ ሥርዓት አልገዛም ያለው ክልል እንደሆነ ብዙዎች ይስማማሉ።

ኢትዮጵያዊ ሆነው፣ ኢትዮጵያዊነትን ለልጆቻቸው አውርሰው፣ ኢትዮጵያን በመምረጣቸው ምክንያት ማንኛውንም መስዋዕትነት ለመቀበል ወስነው፤ ማን እንደላከው ባልታወቀ ቅጥረኛ የተገደሉትን ጄ/ል ሰዓረን ለመሸኘት በተገኘ ሰፊ ቁጥር ያለው ሕዝብ ፊት የጦርነት አዋጅ ስሜት ያለው ንግግር ያቀረበው የትግራዩ ክልል መሪ ንግግሩ የዛቻና የአትንኩን ባይነት ብቻ ሳይሆን የፍርሃቻም ነው በማለት የሚናገሩ አሉ። ፍርሃቻ ደግሞ በቀጣይ በትግራይና በህወሓት ላይ ሊወሰድ ይችላል ተብሎ ከተገመተ እርምጃ የመነጨ ሊሆን ይችላል። በየትኛውም መልኩ ቢወሰድ ህወሃት የጄ/ል ሰዓረን ቀብር ትግራይ በማድረግ የሚዲያ ሽፋን በማግኘት የፈለገውን መልዕክት ለማስተላለፍ ችሏል።

ለጎልጉል አስተያየቷን የሰጠች በሰሜን አሜሪካ የምትኖር አፍቃሪ ህወሓት፤ ጠ/ሚ/ር ዐቢይ ጄ/ል ሰዓረን አስገደለ እየተባለ በማኅበራዊ ሚዲያ “አክቲቪስት ተብዬዎች” ባለቻቸው የሚወራውን በመረረ ቋንቋ ትቃወማለች። “ተገዢ ሆኖ፣ ለዐቢይ ታማኝ ሆኖ፣ የተሰጠውን ተልዕኮ ሁሉ ያለ ተቃውሞ ሲፈጽም የነበረን ሰው (ሰዓረን ማለቷ ነው) ዐቢይ ለምንድነው የሚገድለው? ብርሃኑ ጁላን ኤታማዦር ሹም አድርጎ ለመሾም ነው እየተባለ የሚነገረው ከንቱ ልፍለፋና ከድንቁርና የመነጨ ነው፤ ብርሃኑ ጁላን ለመሾም ሰዓረን የግድ መግደልና አገር ማተራመስ የለብህም፤ ጡረታ አንዱ ነው፤ ሌሎችም መፍትሔዎች አሉ፤ … ” በማለት በእርሷ ዙሪያ የሚገኙ ሰዎች የሚስማሙበትን ሃሳብ ተናግራለች።

በሌላ አንጻር ግን ጄ/ል አበባውን እጅግ የከረሩ ቃላትን በመጠቀም አብዝታ ረግማቸዋለች። “ማን ላይ ጣት ለመቀሰር ነው አፈነዳዋለሁ ያለው? ማንን ተጠርጣሪ ለማድረግ ነው እንዲህ ብሎ የሚናገረው? የሥራውን፣ የእጁን ያገኛታል” በማለት በማያሻማ ሁኔታ ምሬቷን ገልጻለች።

“ከፈለገ ይፈንዳ … ይሄ ለውጥ ከመጣ በኋላ ሰዓረ እንደ ከሃዲ ተቆጠረ፤ በጥቂት ቡድኖች፤ ኢትዮጵያዊነቱ አሳልፎ እንዲሰጥ ከፍተኛ ተፅዕኖ ደረሰበት” በማለት ጄ/ል አበባው ሕዝብ በቀጥታ በሚከታተለው ፕሮግራም ላይ ሳይሸራረፍና ሳይቆራረጥ እንዲሁም የአርትዖት ሥራ ሳይደረግበት መናገራቸው አጀንዳውን በሙሉ በህወሓት ላይ ወርውረውታል። አበባው ለዚህ ዓይነቱ የድፍረትና አጥፊውን አጋልጦ ለሰጠ ንግግራቸው አፍቃሪ ህወሃት የሆነችው አስተያየት ሰጪና ሌሎች መሰሎቿ “የእጁን ያገኛታል” በሚለው ፉከራ ይስማማሉ።

ሳሞራ የኑስን እና አባዱላ ገመዳ

ጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ በዚህ ጉዳይ ላይ ከተለያዩ የማኅበራዊ ድረገጾች ያገኘው መረጃ እንደሚጠቁመው በርካታ የህወሓት ደጋፊዎች በጄ/ል አበባው ላይ የጥላቻ ዘመቻ የከፈቱ መሆናቸውን ለመመለከት ችሏል። የሟች ጓዳቸውን አስከሬን ከፊታቸው እየተመለከቱ ጄ/ል አበባው “ያፈነዱት” መረጃ ይፍጠን ይዘግይም በትግራይ የሚፈነዳ ነገር እንደሚኖር በወዳጃቸው ስም እየማሉ በቃልኪዳን የተናገሩት እንደሆነ ተደርጎ ተወስዷል። አበባው “ይሄ ለውጥ ከመጣ በኋላ ሰዓረ እንደ ከሃዲ ተቆጠረ” እያሉ ይህንን በብዙዎች ዘንድ ያልተጠበቀ ቀስቃሽ ንግግር በሚያደርጉበት ጊዜ ምስል የመቅረጫው ካሜራ የህወሓቱን ሳሞራ የኑስን እና አባዱላ ገመዳን ሲያሳይ ነበር። 

በአዲስ አበባና በባህርዳር ግድያው ከተካሄደ በኋላ ሌላውን ቦምብ በህወሓት ላይ ያፈነዱት በአሜሪካ የውጭ ጉዳይ ሚ/ር መ/ቤት የአፍሪካ ጉዳዮች ኃላፊው ቲቦር ኒጌይ ናቸው። በወቅቱ በደቡብ አፍሪካ ሆነው ስለ ኢትዮጵያ ሁኔታ ይህንን ብለዋል፤ “እንደሚታወቀው ጠ/ሚ/ር ዐቢይ ወደ ሥልጣን ሲመጡ ተከታታይና አስደናቂ ለውጦችን፤ ለምሳሌ በቀጣናው ከኤርትራ ጋር ሰላም በመፍጠር እንዲሁም በአገር ውስጥ፤ አምጥተዋል፤ … ጠ/ሚ/ሩ (ለለውጡ የሚጠቅሙ) የራሳቸውን ሰዎች ወደሥልጣን እያመጡ ነበር፤ … ለምሳሌ አሁን የተገደሉት የአማራ ርዕሰ መስተዳድር የዐቢይ የራሳቸው ሰው ነበሩ፤ በሌሎችም ክልሎች እንዲሁ እየተደረገ ነው፤ በትግራይ ግን ያለው ሁኔታ ለእርሳቸው በጣም አስቸጋሪ ነው፤ ምክንያቱም ክልሉን በደንብ አድርገው የተቆጣጠሩ የቀድሞው አገዛዝ ርዝራዦች አሉ፤  … በኢትዮጵያ በጣም ብዙ ሕዝብ ይህንን ለውጥ/ተሃድሶ ይደግፋል፤ ነገርግን የቀድሞ አገዛዝ (የህወሓት) ርዝራዦች ደግሞ አሁንም አሉ፤ ስለዚህ ቀጣዩ ጉዞ ለዐቢይ ቀላል አይሆንላቸውም፤… ይህ የደረሰው አደጋ የመጨረሻው እንዲሆን እመኛለሁ፤ ነገርግን ማንም እርግጠኛ መሆን አይችልም፤ ምክንያቱም መቼ፣ በማን፣ እና የት ቀጣዩ ሙከራ እንደሚሆን ለማወቅ ያዳግታል፤ አንድ እርግጥ የሆነ ነገር አለ፤ ጠ/ሚ/ሩ ከዚህ በኋላ በሙሉ ኃይል ወደፊት ነው የሚገፉት፤ ያሁኑ ክስተት ወደኋላ ሊጎትታቸው አይችልም”።  

ቲቦር ኒጌይ

ዲፕሎማቱ እንዳሉት የዐቢይ አስተዳደር በሙሉ ኃይል እርምጃ ወደ መውሰድ ይሄዳል ተብሎ ይጠበቃል። ይህም በፊት ሲነገር ከነበረው የፍቅርና የይቅርታ ጉዞ በተለየ መልኩ የፌዴራሉን አመራርና እርምጃ የመውሰድ ብቃት በሚያሳይ መልኩ የሚከናወን ይሆናል።

አዲስ አበባ ሲመጣ እየተደመረ መቀሌ ሲደርስ የሚቀነሰው ደብረፂዮን በዚህ መልኩ የማይቀጥልበት ሁኔታ በአደባባይ ፈንድቷል። በትግራይ ሸምቀው የተቀመጡ ወንበዴዎችና በወንጀል የተጠረጠሩ ለፍርድ ለማቅረብ የሚቻልበት ሁኔታ በብልሃት ካልተሠራበት ረዳት ኃላፊው ቲቦር ኒጌይ እንዳሉት “የቀድሞው አገዛዝ ርዝራዦች” የዘረፉትን ኃብት በመጠቀም ለሌላ ጥቃት ሳይዘጋጁ የጄኔራል አበባው ታደሰ “ከፈለገ ይፈንዳ” ንግግር በትግራይ ሌላ ቦምብ እንዳያፈነዳ በህወሓት ዘንድ ቀዳሚ አጀንዳ ሆኖ ተወስዷል። በቲቦር ኒጌይ አገላለጽ ከዚህ በኋላ ምንም አይጎትታቸውም የተባለላቸው ጠ/ሚ/ር ዐቢይ አህመድ በሙሉ ኃይል ወደፊት መግፋት ይጠበቅባቸዋል።  


EmbassyMedia - ራብዓይ ግንባር!

Dehai Events