አዲስ አበባ፣ ነሃሴ 17፣ 2018 (ኤፍ.ቢ.ሲ) በኤርትራው ፕሬዚዳንት ኢሳያስ አፈወርቂ የሚመራ የልኡካን ቡድን ወደ አማራ ክልል እንደሚመጣ ተገለፀ።
የአማራ ክልል መንግስት ኮሙዩኒኬሽን ጉዳዮች ቢሮ ሀላፊ አቶ ንጉሱ ጥላሁን የሚመሩት ልኡክ በአስመራ ይገኛል።
በቆይታቸውም አቶ ንጉሱ ጥላሁን ከፕሬዚዳንት ኢሳያስ አፈወርቂ ልዩ አማካሪ ከአቶ የማነ ገብረአብ ጋር የኤርትራውያንንና የኢትዮጵያዊውያንን የሕዝብ ለሕዝብ ግንኙነት ማጠናከር በሚቻልበት ላይ መወያየታቸውን አስታውቀዋል።
በዚህም መሠረት በቅርቡ በአማራ ብሔራዊ ክልል ምክር ቤት አፈ ጉባኤ የሚመራ የልዑካን ቡድን ወደ አስመራ እንዲጓዝ መስማማታቸውንም አቶ ንጉሱ ገልፀዋል።
እንዲሁም የኤርትራው ፕሬዚዳንት ኢሳያስ አፈወርቂ የሚመሩት የልዑካን ቡድን ወደ አማራ ክልል እንዲሚመጣ ከስምምነት መድረሳቸውም አቶ ንጉሱ ያስታወቁት።
በአማራ ክልል በተለይም በጎንደርና በባህር ዳር በርካታ ኤርትራውያን ይኖራሉ ያሉት አቶ ንጉሱ፥ በ2011 ዓ.ም. ከተለያዩ የሀገሪቱ ብሔር ብሔረሰቦች እና ሕዝቦች በተለይም ከአጎራባች ክልሎች ጋር ጠንካራና ተከታታይ የሕዝብ ለሕዝብ ግንኙነት በማካሄድ አገራዊ አንድነትን ለማጠናከር እንደሚሰራም ገልፀዋል።
አቶ ንጉሱ አክለውም በአስመራ ቆይታቸው፥ መቀመጫውን ኤርትራ ያደረገው የአማራ ዴሞክራሲያዊ ሀይል ንቅናቄ ወደ አማራ ክልል ገብቶ በሚንቀሳቀስበት ሁኔታ ላይ በመወያየት ከስምምነት ላይ መድረሳቸውንም አስታውቀዋል።