World News

Goolgule.com: የሜቴኩ ክንፈ እና የኢንሳው ተክለብርሃን በቁጥጥር ሥር ውለዋል የሌሎች የቀድሞ ህወሓት አባላትም ለፍርድ እንደሚቀርቡ ተነገረ

Posted by: Berhane.Habtemariam59@web.de

Date: Tuesday, 13 November 2018

የቀድሞው የሜቴክ ዋና ኃላፊ የነበረው ክንፈ ዳኜው እና የኢንሳ (የህወሃት የኢንፎርሜሽን ስለላ) ኃላፊ የነበረው ተክለብርሃን ወልደአረጋይ በቁጥጥር ሥር መዋላቸውን የአማራ ብዙሃን መገናኛ ድርጅት (አብመድ) በፌስቡክ ገጹ ምንጮቹን ጠቅሶ አስታውቋል።

ዋልታ እንደዘገበው ደግሞ “ሱዳን ድንበር አካባቢ የተያዙት ሁለቱ ተጠርጣሪ ግለሰቦች ዛሬ (ማክሰኞ) ከሰአት ወደ አዲስ አበባ እንደሚገቡ የደረሰን መረጃ ያመለክታል”።

አብመድ ግለሰቦቹን በስም ባይጠቅስም በዜናው ላይ ግን “የብረታ ብረት እና ኢንጂነሪንግ ኮርፖሬሽን (ሜቴክ) እና የኢንሳ የቀድሞ ኃላፊዎች በቁጥጥር ሥር ውለዋል” በማለት ነበር የዘገበው።

ጠቅላይ ዐቃቤ ሕግ ትላንት በሰጠው መግለጫ ሜቴክ ያለምንም ጨረታ የ37 ቢሊዮን ብር ግዢ የፈጸመ መሆኑን የተናገረ ሲሆን በሽብር፣ በሰብዓዊ መብቶች ጥሰት እና በሙስና ወንጀሎች የተጠረጠሩ 63 ግለሰቦች እና ኃላፊዎች በቁጥጥር ሥር መዋላቸውን ማስታወቁ ይታወሳል።

ከህወሓት የሚያፈተልኩ መረጃዎች ይፋ በማውጣት በአብዛኛው የሚታወቀው ስዩም ተሾመ ደግሞ በፌስቡክ ገጹ “ጄ/ል ክንፈ ዳኘው እና ጄ/ል ተክለብርሃን ወልደአረጋይ ወደ ሱዳን ለማምለጥ በመሸሽ ላይ እያሉ ማታ ከምሽቱ 5:00 ሰዓት ላይ በቁጥጥር ሥር መዋላቸውን ለማረጋገጥ ተችሏል” በማለት ጽፏል።

ክንፈ እና ተክለብርሃን በትላንትናው ቀን ወልቃይት ገብተው እንደነበር በማኅበራዊ ድረገጾች ተዘግቦ የነበረ ሲሆን ከዚሁ ጋር ተያይዞ ተሳፍረውበታል የተባለውን መኪና ፎቶ ጭምር አብሮ ተለቅቆ ነበር።

ጠ/ሚ/ር ዐቢይ አሕመድ ወደ ሥልጣን ከመጡ በኋላ ሁለቱ የህወሓት ቀኝ እጆች ከቀድሞው ኃላፊነታቸው በመነሳት ወዲያውኑ ወደ መቀሌ ከትመው እንደነበር ይታወሳል። እዚያም ሆነው የተለያዩ ቃለምልልሶችንና መረጃዎችን በመልቀቅ የለውጡን አካሄድ ለማጨናገፍ በርትተው ሲሠሩ እንደነበር ይታወቃል። አንዳንዶችም በተለያዩ የኢትዮጵያ ቦታዎች የሚነሱ ግጭቶችን በማስተባበር፣ በገንዘብ በመርዳት፣ መሣሪያ በማቀበል፣ ወዘተ ሁለቱ ሰዎች ቁልፍ ሚና ነበራቸው በማለት ይናገራሉ።

በቀጣይ ሌሎች የህወሓት የቀድሞ ሹማምንት ለፍርድ የሚቀርቡበት ሁኔታ እንደሚኖር ጎልጉል ከተለያዩ ምንጮቹ ያገኘው መረጃ ያመለክታል።

እንደሌሎቹ ከዕውቀት የጸዱ የህወሓት ወንበዴዎች፤ ያለ ዓቅማቸው የጄኔራልነት ማዕረግ የተሸከሙት ሁለቱ ግለሰቦች በበርካታ ወንጀሎች የሚጠየቁ ሲሆን ተክለብርሃን ጄኔራልነቱ አልበቃ ብሎት ከዲግሪ ወፍጮ ቤት እንደ ማንኛውም የህወሓት ወንበዴ የዶክትሬት ዲግሪ መግዛቱ ይታወቃል።

ጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ

ከዚህ ጋር በተያያዘ የፌደራል ጠቅላይ አቃቤ ህግ እስካሁን በቁጥጥር ስር የዋሉ ግለሰቦችን ዝርዝር ይፋ ማድረጉን ፋና ዘግቧል።

በዚህም መሰረት በሰብዓዊ መብት ጥሰት ተጠርጥረው በቁጥጥር ስር የዋሉት፦

  1. አቶ ጉሃ አጽበሃ ግደይ – የአዲስ አበባ የደህንነት ኃላፊ
  2. አቶ አማኑኤል ኪሮስ መድህን – የሃገር ውስጥ ደህንነት ጥበቃ ዋና መምሪያ ዳይሬክተር
  3. አቶ ደርበው ደመላሽ – የውስጥ ደህንነት ምክትል ዋና ዳይሬክተር የነበሩና የኢኮኖሚ ጉዳዮች መምሪያ ኃላፊ
  4. አቶ ተስፋዬ ገብረጻዲቅ – የውስጥ ደህንነት ጥናትና የወንጀል ምርመራ መምሪያ ኃላፊ
  5. አቶ ቢኒያም ማሙሸት – በውስጥ ደህንነት ጥበቃ ዋና መምሪያ የኦፕሬሽን ጉዳይ መምሪያ ኃላፊ (በዋናነት የግንቦት 7 ጉዳይ ክትትል)
  6. አቶ ተሾመ ሀይሌ – የአማራ ክልል የደህንነት ኃላፊ የነበሩና የጥበቃ ዋና መምሪያ ዳይሬክተር
  7. አቶ አዲሱ በዳሳ – በሃገር ውስጥ ደህንነት የኦሮሚያ ክልል ደህንነት ኃላፊ
  8. አቶ ዮሃንስ ወይም ገብረእግዚአብሄር ውበት – የውጭ መረጃ
  9. አቶ ነጋ ካሴ – በጸረ ሽብር መምሪያ የኦነግ ክትትል ኃላፊ
  10. አቶ ተመስገን በርሄ – በጸረ ሽብር መምሪያ የኦነግና ኦብነግ ክፍል ዋና ኃላፊ
  11. አቶ ሸዊት በላይ – በሃገር ውስጥ ደህንነት ኦፕሬሽን መምሪያ የግንቦት 7 ክትትል ምክትል መምሪያ ኃላፊ
  12. አቶ አሸናፊ ተስፋሁን – በሃገር ውስጥ ደህንነት የአማራ ክልል ሰሜን ጎንደር ዞን ደህንነት አስተባባሪ
  13. አቶ ደርሶ አያና – በውጭ መረጃ የአማራ ክልል ክትትል
  14. አቶ ሰይፉ በላይ – በውስጥ ደህንነት የደቡብ ክልል ክትትል ኦፊሰር
  15. አቶ ኢዮብ ተወልደ – በውስጥ ደህንነት የደቡብ ክልል ደህንነት ኃላፊ
  16. አቶ አህመድ ገዳ – በውስጥ ደህንነት የኦሮሚያ ክልል ክትትል ምክትል ኃላፊ
  17. ምክትል ኮማንደር አለማየሁ ሀይሉ ባባታ – ቀድሞ የፌደራል ፖሊስ የሽብር ወንጀል ምርመራ ምክትል ዳይሬክተር የነበረና ዋና ዳይሬክተር ሆኖ ያገለገለ
  18. ምክትል ኢንስፔክተር የሱፍ ሀሰን – የሽብር ወንጀል መርማሪ
  19. ዋና ሳጅን እቴነሽ አራፋይኔ – የሽብር ወንጀል መርማሪ
  20. ኢንስፔክተር ፈይሳ ደሜ – የሽብር ወንጀል መርማሪ
  21. ምክትል ኢንስፔክተር ምንላርግልህ ጥላሁን – የሽብር ወንጀል መርማሪ
  22. ዋና ሳጅን ርዕሶም ክህሽን – የሽብር ወንጀል መርማሪ
  23. ኦፊሰር ገብረማሪያም ወልዳይ
  24. ኦፊሰር አስገለ ወልደጊዮርጊስ
  25. ዋና ሱፐር ኢንቴንደንት አሰፋ ኪዳኔ
  26. ዋና ሱፐር ኢንቴንደንት ገብረ እግዚአብሔር ገብረሐዋርያት – የቂሊንጦ ማረሚያ ቤት የጥበቃና ደህንነት ኃላፊ
  27. ዋና ሱፐር ኢንቴንደንት ተክላይ ኃይሉ – የቂሊንጦ ማረሚያ ቤት ሰራተኛ
  28. ዋና ሱፐር ኢንቴንደንት አቡ ግርማ – የሸዋ ሮቢት ማረሚያ ቤት ኃላፊ የነበረና በዝዋይ ማረሚያ ቤት ኃላፊ ሆኖ ሲያገለግል የነበረ
  29. ዋና ሱፐር ኢንቴንደንት አዳነ ሐጎስ – የቃሊቲ ማረሚያ ቤት ሰራተኛ
  30. ዋና ሱፐር ኢንቴንደንት ተስፋሚካኤል አስጋለ – በቃሊቲ ማረሚያ ቤት ከፍተኛ የደህንነት ባለሙያ
  31. ዋና ሱፐር ኢንቴንደንት ገብራት መኮንን – የዝዋይ ማረሚያ ቤት የጥበቃና ደህንነት ኃላፊ የነበረና የሸዋ ሮቢት ማረሚያ ቤት ጥበቃና ደህንነት ኃላፊ ሆኖ ሲያገለግል የነበረ
  32. ረዳት ኢንስፔክተር አለማየሁ ኃይሉ ወልዴ – በአዲስ አበባ ፖሊስ የወንጀል መርማሪ
  33. ረዳት ኢንስፔክተር መንግስቱ ታደሰ አየለ – በአዲስ አበባ ፖሊስ የወንጀል መርማሪ
  34. አዳነች ወይም ሃዊ ተሰማ ቶላ
  35. ጌታሁን አሰፋ ቶላ
  36. ሙሉ ፍሰሃ

(ባሃሩ ይድነቃቸው)


EmbassyMedia - ራብዓይ ግንባር!

Dehai Events