World News

Ethsat.com: የኢሕአዴግ ስራ አስፈጻሚ ኮሚቴ ስብሰባ በውጥረት መቀጠሉ ተሰማ

Posted by: Berhane Habtemariam

Date: Tuesday, 13 March 2018

(ኢሳት ዲሲ–መጋቢት 4/2010)

March 13, 2018

አዲስ ጠቅላይ ሚኒስትር የመምረጡ ሂደት በፈጠረው ውዝግብ ጠቅላይ ሚኒስትር የመሰየሙ ሒደት ላልተወሰነ ጊዜ እንዲራዘም ሃሳብ መቅረቡም ተመልክቷል።

በሕወሃት ሰዎች እንዲሁም ከብአዴን አቶ በረከትና ተከታዮቻቸው ከህወሃት ጎን በመሰለፍ ኦሕዴድን በማጥቃት ላይ መሆናቸውም ተመልክቷል።

እሁድ የተጀመረውና የድርጅቱን ሊቀመንበር መምረጥን በዋናነት አጀንዳ ያደረገው የኢሕአዴግ ስራ አስፈጻሚ ኮሚቴ ስብሰባ እንደተጠበቀው የድርጅቱን ሊቀመንበር ለፓርቲው ምክር ቤት ማቅረቡ አጠራጣሪ ሆኗል።

በብዙዎች ዘንድ የሚጠበቁትንና ምዕራባውያንም በተለይም ዩናይትድ ስቴትስ አሜሪካ ጭምር በመፍትሄነት ያቀረበቻቸውን ዶክተር አብይ አሕመድን የሕዝባዊ ወያኔ ሃርነት ትግራይ/ሕወሃት/ሰዎች በፍጹም የሚቃወሙ ሆነው ተገኝተዋል።

በአቶ በረከት ግንባር ቀደምትነት የብአዴን ከፊል አባላትም የሕወሃትን መስመር በመደገፍ ከዶክተር አብይ አሕመድ በተቃራኒ መቆማቸውም ተመልክቷል።

የደኢሕዴን አባላትም እንደ ሕወሃት ሙሉ በሙሉ ሊባል በሚችል ደረጃ የዶክተር አብይ አህመድን መመረጥ በመቃወም እየተሳተፉ መሆናቸውም ተመልክቷል።

ዘግይተው የሚወጡ መረጃዎች እንደሚያመለክቱት የኦሕዴድ ሊቀመንበር እንዲሁም ጠቅላይ ሚኒስትር የመምረጡ ሁኔታ ላልተወሰነ ጊዜ እንዲራዘም በአቶ በረከት ስምኦን የቀረበው ሃሳብ ተቀባይነት እያገኘ መቷል።

አቶ በረከት የሚያቀነቅኑት ይህ የጠቅላይ ሚኒስትሩ የምርጫ ጊዜ ይራዘም ሃሳብ በትንሹ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ እስኪያበቃና እስከ ኢሕአዴግ ጉባኤ ድረስ እንዲቆይ  መሆኑም ታውቋል።

በአቶ በረከት አንደበት የሚቀነቀነው ይህ ሃሳብ ከሕወሃት መሪዎች ጋር ስምምነት የተደረሰበት እንደሆነም ምንጮቹ ይገልጻሉ።

ይህም በቀጣዮቹ ስድስት ወራት በአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ ኮማንድ ፖስት የኦሮሚያ ክልል የኦሕዴድን መዋቅር ካፈራረሱና እነ አቶ ለማን ካንሳፈፉ በኋላ የሚፈልጉትን ሰው ለመምረጥ እንደሆነም መረዳት ተችሏል።

ለቀጣዮቹ 6 ወራት ስፍራውን ክፍት አድርጎ መሔዱ ከአለም አቀፉ ማህበረሰብ ጭምር ያልተጠበቀ ውግዘት ያስከትላል የሚሉ አንዳንድ የህወሃት መሪዎች መኖራቸውም ታውቋል።

ከኦሕዴድ አቶ አባዱላ ገመዳን ወይንም ዶክተር ወርቅነህ ገበየሁን በመምረጥ በእነሱ ጭምር እገዛ በኮማንድ ፖስቱ ስር የኦሕዴድን መዋቅር አፈራርሶ እንደገና ማደራጀት ይቻላል የሚለውን አነሰተኛው የሕወሃት ድምጽ  በሕወሓት ውስጥ  እየተነሳ መሆኑንም የሚገልጹ ወገኖች አሉ።

ሆኖም ስብሰባው አሁንም በዝግ በመቀጠሉ የትኛው ሃሳብ ተቀባይነት አግኝቶ እንደሚወጣ እየተጠበቀ ይገኛል።


EmbassyMedia - ራብዓይ ግንባር!

Dehai Events