World News

Goolgule.com: የመለስ “ሌጋሲ” በአዜብ መታገድ መቃብር ገባ

Posted by: Berhane Habtemariam

Date: Tuesday, 28 November 2017

የመለስ “ሌጋሲ” በአዜብ መታገድ መቃብር ገባ

  • ህወሓትን ለመምራት ደብረጽዮን፣ ዓለም፣ ጌታቸውና ፈትለወርቅ ታጭተዋል

እርስበርሱ ሲነታረክ የቆየው የህወሓት ግምገማ አባይ ወልዱን በማባረርና አዜብ መስፍንን በማገድ እርምጃ መውሰዱ ታውቋል። እነደብረጽዮን የሚመሩት የማጽዳት ዘመቻ በመለስ “ሌጋሲ” ላይ አብሮ እርምጃ ወስዷል። የመሪነቱን ቦታ ፈትለወርቅ፣ ደብረጽዮን፣ ጌታቸውና ዓለም እየተፎካከሩበት ነው ተብሏል።

አፍቃሪ ህወሓትና የህወሓት ልሳን ከሆኑ የዜና ምንጮች በቀረበው መረጃ መሠረት ሰሞኑን በግምገማ እርስበርሱ ሊበላላ ደርሶ የነበረው የህወሓት ግምገማ “ቆራጥ” እርምጃዎችን ወስዷል። በዚህም መሠረት በመለስ ዜናዊ ምትክ የ“ወንበዴ” ድርጅቱ ኃላፊ ሆኖ ሲሠራ የነበረው አባይ ወልዱ ከሊቀመንበርና ሌሎች ከፍተኛ ኃላፊነቶች ተወግዶ በተራ አባልነት እንዲቀጥል ተወስኖበታል።

ከአባይ መሰናበት በተጨማሪ “አዜብን መንካት የመለስ ሌጋሲን አደጋ ላይ መጣል ነው” በሚል እንድምታ በግዱ ለአዜብ ሲያጎነብስ የነበረው ትግራይን ለመገንጠል የተቋቋመው ቡድን አዜብን ከከፍተኛ ኃላፊነቷ አንስቷታል። ከቀናት በፊት አዜብንና ተላላኪዎቿን ለመቀርጠፍ ግምገማው ሲጣደፍ በነበረበት ጊዜ አዜብ መስፍን ስብሰባውን ረግጣ መውጣቷ ይታወቃል። ለዚህ ድርጊቷ በተደጋጋሚ ይቅርታ ብትጠይቅም ሆነ ደብዳቤ ጽፋ ብታስገባም “ኃጢአቷን ካናዘዘ” በኋላ በዕገዳው ጸንቷል።

“ባለራዕዩ መሪ” እየተባለ ሲሞገስና ሲሞካሽ የኖረው መለስ በሙት መንፈስ አገሪቱን ሲመራ መቆየቱ የሚታወቅ ነው። ሞት እንደ ቡሽ ክዳን በድንገት ቢያስፈነጥረውም ህወሓት በእርሱ መንፈስ እመራለሁ ሲል አዜብም “አንዲት ሓሳብ ይዞ ወደ ምድር” የመጣውን ሙት ባሏን ከለላ በማድረግ ያሻትን ስትናገርና ስትከውን ላለፉት አምስት ዓመታት ቆይታለች።

መለስ ከመሞቱ 3ዓመት በፊት በአሜሪካ ከአውሮጵላን ለመውረድ ሲችገር

በህወሓት ነባር ወንበዴዎች ዘንድ በንቀት የምትታየው አዜብ ከመለስ ሞት በኋላ ከማንኛውም ኃላፊነት እንድትወገድ ሲሞከር ቆይቷል። ሆኖም እርሷን በሙስና ወይም በሌላ ሰበብ ማባረር በመለስ ውርስ (ሌጋሲ) ላይ ትልቅ ጥያቄ ያስነሳል በሚል ውሳኔው ተግባራዊ ሳይደረግ ቆይቷል። በሙስና ከተባረረች የሙስናው እፍታ ለመለስም ደርሷል የሚለው አስተሳሰብ የባለራዕዩን መሪ ስም የሚያጠለሽ ነው የሚል አስተያየት ሲሰጥበት ቆይቷል። በኪራይ ሰብሳቢነት ወይም በችሎታ፣ በአቅም ማነስ ወይም በአስተሳሰብ ደካማነት ወይም በሥልጣን መባለግ በሚሉ ሰበቦች ብትባረር ያለ ችሎታዋና ያለ አቅሟ ወደ ሥልጣን እንድትመጣ ያደረገውን መለስ አሁንም የሚያዋርድ ነው በሚል ጥርስ ሲነከስባት ሰንብቷል።

በህወሓት ጉዳይ ውስጥ አዋቂ ነን የሚሉ እንደሚናገሩት አዜብ መታገድ ብቻ ሳይሆን ሙሉ በሙሉ ከድርጅቱ ትባረራለች የሚል አስተያየት እየሰጡ ናቸው። ይህ በሚሆንበት ጊዜ ደግሞ ከእርሷ ጋር አብሮ የመለስ ሌጋሲ በዜሮ እንዳባዛ ጥንቃቄ መደረግ እንዳለበት ያሳስባሉ። በመሆኑም እስካሁን የአዜብን ጉዳይ በትዕግስት ሲያስታምም የቆየው ህወሓት አዜብ የምትባረረው ከመለስ ሞት በኋላ በፈጸመችው ስህተት መሆኑን በማጉላት የመለስን “ሌጋሲ” ለማዳን የፕሮፓጋንዳ ሥራ የመሥራት ዕቅድ ያስፈልጋል የሚሉ ወያኔዎች የሚሰጡት አስተያየት አብላጫነት እያገኘ መጥቷል።

አዜብን በማገድ፣ በየነ ምክሩንና አባይ ወልዱን በማባረር የቀጠለው የትግራይ ህዝብ ነጻ አውጪ ግምባር (ህወሓት) ግምገማ በተባረሩት ምትክ አዳዲስ አባላትን ያስገባል። በዓለምአቀፋዊ የመረጃ ቋት በአሸባሪነት ለተመዘገበው ድርጅት – ህወሓት – መሪ ይመርጣል። ሁለቱ የደኅንነትና የስለላ ማሽኖች ደብረጽዮን ገብረሚካኤልና ጌታቸው አሰፋ እንዲሁም ዓለም ገብረዋህድ ለመሪነት ቀዳሚ ተፎካካሪዎች እንደሆኑ የህወሓት ተላላኪዎች ቢናገሩም በበረሃ ስሟ “ሞንጆርኖ” እየተባለች የምትጠራው ፈትለወርቅ ገብረእግዚአብሔር ቀጣይዋ የህወሓት መሪ እንደምትሆን ስዩም ተሾመ ምንጮቼ አረጋግጠውልኛል በማለት በፌስቡክ ገጹ ላይ ዘግቧል።


EmbassyMedia - ራብዓይ ግንባር!

Dehai Events