Dehai News

Satenaw.com: በግምት ወደ ኤርትራ እያስደወለ ያለው ናፍቆት

Posted by: Berhane.Habtemariam59@web.de

Date: Wednesday, 11 July 2018

አዲስ አበባ፣ሃምሌ፣4፣2010 (ኤፍ.ቢ.ሲ) በኢትዮጵያና ኤርትራ መካከል የስልክ ግንኙነት ከ20 ዓመታት በኋላ መጀመሩን ተከትሎ ኢትጵያውያን በግምት ወይም በዘፈቀደ ወደ ኤርትራ ስልክ እየደወሉ መሆኑን ሲ ኤን ኤን አስነብቧል።

ሁለቱ በባህል፣ ቋንቋ እና በማህበራዊ ጉዳዮች የሚተሳሰሩትና ከ20 ዓመታት በኋላ ግንኙነታቸውን ያደሱት የኢትዮጵያና ኤርትራ ጉዳይ በርካታ አለም አቀፍ መገናኛ ብዙሃን ትኩረትን እንደሳበ ቆይቷል።

ሲ ኤን ኤንም በዛሬው የአፍሪካ ገፁ በተለየ ሁኔታ የሀገራቱ ዜጎች ምን ያህል እንደተነፋፈቁና ምን ያህል የተቀራረቡ ህዝቦች እንደሆኑ ለማሳየት የሞከረበትን ሀሳብ አስቀምጧል።

ፍሬህይወት ነጋሽ የተባለች የ33 ዓመት ወጣት በትዊተር ገጿ ያሰፈረችውን ሀሳብ የጠቀሰው ሲኤን ኤን በዘፈቀደና በግምት ወደ ኤርትራ ስልክ እንደደወለችና ስልኩን የመለሰችላትም ኤርትራ ወደሚገኝ ክሪስታል ሆቴል እንደደወለች አረግጣልኛለች ማለቷን አስነብቧል።

ፍሬህይወት በግምት የደወለችው ስልክ ሲነሳላት ከኢትዮጵያ እንደደወለች በመግለፅ እንኳን ደስ አላችሁ መልዕክትና ደስተኛ መሆኗን የገለፀች ሲሆን ፥ በተመሳሳይ ስልኩን የመለሰችላት ደስተኛ መሆን እንደገለፀችላት በገጿ አስፍራለች።

ወጣቷ ከዚህ ዓመት በኋላ ኤርትራን ለመጎበኘት እቅድ እንዳላትም ተናግራለች።

ፍሬህይወት ወደ ኤርትራ የሚደረገው የስልክ አገልገሎት መጀመሩን ለማረጋገጥ ከደወሉ በርካታ ኢትዮጵያውን መካከል እንደምትጠቀስ ያስነበበው ሲ ኤን ኤን እሷን ጨምሮ በርካታ ኢትዮጵያውያን ለበርካታ ዓመታት ሲናፈቋቸው የነበሩ ጓደኞች እና ቤተሰቦች እየደወሉ ተገናኝተዋል ብሏል።

ሄኖክ ካርቮኔን የተባለው ሌላው ኢትዮጵያዊ በትዊተር ገፁ በግምትና በዘፈቀደ ወደ ኤርትራ በደወለበት ወቅት ፍርቱና ከተባለች ኤርትራዊት ጋር በአማረኛ ማውራቱን አስፍሯል።

ሄኖክ በኢትዮጵያ እና በኤርትራ መከካል እየታየ ያለው የለውጥ መንፈስ እና መተባበር በእጅጉ እንዳስገረመው ገልጿል።

በሀገራቱ መካከል ተቋርጦ የነበረው የስልክ ግንኙነት ከ20 ዓመታት በኋላ መጀመሩን ያስታወሰው ገፁ ኢትዮ ቴሌኮም ለ57 ሚሊየን ደንበኛቹ በአጭር የፁህፍ መልዕክት በሀገራቱ መካከል የስልክ ግንኙነት መጀመሩን እንዳስታወቀ ዘግቧል።


በኤፍሬም ምትኩ


EmbassyMedia - ራብዓይ ግንባር!

Dehai Events