Goolgule.com: የኢሬቻ የጅምላ ጭፍጨፋ ሃውልት እንዲሰራ ሃሳብ ቀረበ:: የህወሃት ጠላትነት በየዓመቱ ይዘከራል

From: Berhane Habtemariam <Berhane.Habtemariam59_at_gmx.de_at_dehai.org>
Date: Thu, 6 Oct 2016 18:54:09 +0200

የኢሬቻ የጅምላ ጭፍጨፋ ሃውልት እንዲሰራ ሃሳብ ቀረበ

የህወሃት ጠላትነት በየዓመቱ ይዘከራል
irreecha-remember
 
 

የትግራይ ህዝብ ከማን አገዛዝ ነጻ እንዲወጣ እንደሚፈለግ በውል ባይታወቅም ራሱን “የትግራይ ህዝብ ነጻ አውጪ ግንባር” የሚለው ህወሃት በቢሾፍቱ ሰላማዊ ዜጎች ላይ ያካሄደው የጅምላ ጭፍጨፋ የሚዘክር ሃውልት እንዲቆም ሃሳብ መቀረቡ ተሰማ። የኢሬቻን ክብረ በዓል ለማክበር የተሰባሰቡ የኦሮሞና የሌሎች ቦታዎች ተወላጆች ላይ የተፈጸመውን የጅምላ ጭፍጨፋ ትውልድ ሁሉ በማንና እንዴት እንደተፈጸመ እንዲያውቅ፣ እንዲማርና የተከፈለው ዋጋ ምን ያህል እንደሆነ እንዲረዳ፣ እንዲሁም ምስክር ሊሆን በሚያስችለው መልኩ ሃውልቱ እንደሚታነጽ ለማወቅ ተችሏል።

ለመብታቸው የተነሱና በሰላማዊ መንገድ የትግራይ ነጻ አውጪ ግንባርን “በቃህ፣ ልቀቀን” በማለታቸው የኦሮሞ ተወላጆች ላለፉት አስራ አንድ ወራት ሲገደሉ፣ ሲታሰሩ፣ ሲገረፉና ሲሰቃዩ መቆይታቸው ይታወሳል። ባለፈው ሳምንት ቢሾፍቱ የኢሬቻን ክብረ በዓል ላይ በተገኙ ኢትዮጵያውያን ዜጎች ላይ የተፈጸመው ግን አእምሮ ያላቸው ሁሉ ሊቀበሉት ያልተቻላቸው የግፍ ሁሉ ግፍ ሆኖ ተመዝግቧል።irreecha80

በሰላማዊ መንገድ ተቃውሞ ባሰሙ ወገኖች ላይ የደረሰው ይህ ታሪክ የማይረሳው ጭፍጨፋ ያስቆጣው ድፍን የኢትዮጵያን ህዝብ ነው። ክልል፣ ቦታ፣ ዘር፣ አካባቢና እምነት ሳይለይ ድፍን አገርን እንባ ያራጨው የጅምላ ጭፍጨፋ ያላሳዘነው የህዝብን ጩኸት “አንሰማም” ላሉት ክፍሎችና ድርጅታቸው ብቻ መሆኑ ደግሞ ሃዘኑን የከፋ እንዳደረገው በተለያዩ ዘዴዎች የሚወጡ የህዝብ አስተያየቶች ያረጋግጣሉ።

አንድም ጉዳት ያላደረሱ፣ ለማድረስም ባልሞከሩ በሚሊዮን የሚቆጠሩ ንጹሃን ዜጎች ላይ የህወሃት አንጋቾች በመርዝና በጥይት ያደረሱት ዘገናኝ ጭፍጨፋ በታሪክ ሁሉ ሲታወስ እንዲኖር በኦሮሞ ተወላጆች ዘንድ መግባባት አለ። ሌሎች የኅብረተሰብ ክፍሎችም ድጋፍ እንደሚሰጡ ማቅማማት የለም። ለጎልጉል ሃሳባቸውን የሰነዘሩ የስዊትዘርላንድ ነዋሪና የብሄሩ አባል “አሁን ቅድሚያ የሚሰጣቸው የነጻነት ስራዎች ቢኖሩም የዚህ ጭፍጨፋ ሰነድና መረጃዎች በጥንቃቄ ይከማቻሉ” ብለዋል። ሃውልቱ ህወሃት ያልተፈጠረ ታሪክ እየሠራ ሕዝብን ለመከፋፈል እንደተጠቀመባቸው ሳይሆን በመረጃና በማስረጃ የተደገፈ እንደሚሆን ተነግሯል።

ሌላ የሚኖሶታ ነዋሪ  የኦሮሞ ተወላጅ “ህወሃትና የኦሮሞ ህዝብ መካከል ለሚኖረው ግንብ  የሃውልቱ መሰራት ለትውልድ የሚዘልቅ መልስ ነው” ብለዋል። በማህበራዊ ገጾችም “ተስፋ ቁረጡ፣ ካሁን በኋላ እርቅ ጠይቆ ኦሮሞ ላይ ቁማር መጫወት አይቻልም” በሚል ስሜታቸው የመረረ መሆኑንን የሚገልጹ ቁጥራቸው ቀላል አይደለም።

የጅምላ ጭፍጨፋውን ተከትሎ በሚኖሶታ የኦሮሞ ተወላጆች ባካሄዱት አስቸኳይ ስብሰባ ላይ “ህዝብ እየጨፈጨፉ ዛፍ ሥር በመቀመጥ ይቅርታ መጠየቅ ያከተመበት አስተሳሰብ ነው” ሲሉ አቶ ጃዋር መሐመድ ተናግረዋል። ተሰብሳቢዎቹም በጭብጨባ ተቀብለውታል። አሁን ትግሉ የደረሰበት ደረጃ ወደፊት የመጓዝ ብቻ እንደሆነም ተጠቁሟል።

የሃውልቱ መገንባት ዋና አስፈላጊነት ግፍን ለማስታወስና ሁልጊዜ አንድን ወገን እየወቀሱ ለመኖር ሳይሆን ተመሳሳይ የመብት ጭቆና በድጋሚ እንዳይደርስ የተከፈለውን መስዋዕትነት በማሰብ እንዳይደገም ለማስተማር ነው ተብሏል። ከንግዲህ ወዲህ የኢሬቻ በዓል የሚከበረው ህወሃት የፈጸመውን ይህንን ጭፍጨፋ ሳይዘከር ስለማይሆን በሃውልቱ ጉዳይ ላይ ተጎጂ ወገኖች በሙሉ እንዲተባበሩ ሃሳብ ተሰጥቷልተነግሯል።

Received on Thu Oct 06 2016 - 11:33:14 EDT

Dehai Admin
© Copyright DEHAI-Eritrea OnLine, 1993-2013
All rights reserved