Goolgule.com: የቂሊንጦ እስር ቤት ቃጠሎ ለህወሃት ፈተና ተጨማሪ ነዳጅ ሆነ!! “የሚኒስትር ዴኤታዎች እጅ አለበት”

From: Berhane Habtemariam <Berhane.Habtemariam59_at_gmx.de_at_dehai.org>
Date: Sun, 4 Sep 2016 12:03:15 +0200

የቂሊንጦ እስር ቤት ቃጠሎ ለህወሃት ፈተና ተጨማሪ ነዳጅ ሆነ!!

“የሚኒስትር ዴኤታዎች እጅ አለበት”
kilinto prison
 
 

የኢትዮጵያ ፖለቲካ ቀውስ ከቀን ወደቀን እየጋመ ነው። ህወሃት ችግሮችን በሰከነ መንፈስ ከመፍታት ይልቅ ክተት አውጆና ንጹሃንን እየፈጀ ይገኛል። ሥልጣን ከያዙ ጀምሮ የረባ ትዕዛዝ ሰጥተው የማያውቁት ሃይለማርያም “አዝዣለሁ” ሲሉ በወገኖቻቸው ላይ ሞት አውጀው ቀውሱን አግመውታል። አፍቃሪ ህወሃቶችም የ“ቅምጡን ባሪያ ጠቅላይ ሚኒስትር” “ትዕዛዝ” ተከትለው “ትዕግስትም ገደብ አለው” እያሉ በየሚዲያውና በማህበራዊ ገጾች እያሽካኩ ነው። ሕዝብ “መሳሪያ አጣን” እያለ ጥሪ እያቀረበ ነው። ያም ሆኖ ምሬት የገፋቸው ሁሉ አመጹን ገፍተውበታል።

በከፋፍለህ ግዛ የፖለቲካ ቁማር ህዝብ እያናከሰ ላለፉት 25 ዓመታት አገር ሲገዛ የኖረው ህወሃት ዛሬ አደረጃጀቱና “አጋሬ” የሚላቸው የተለዩት ይመስላሉ። ኦህዴድ ከተናጋና ከከዳ ሰንብቷል። ብአዴንም መመኪያ ሊሆን የማይችልበት ደረጃ ደርሷል። ለዚህም ይመስላል በይፋ ባይታወጅም ሁለቱ ክልሎች በወታደራዊ አስተዳደር ሥር ወድቀዋል

በተለይ የአማራ ክልል ሙሉ በሙሉ በወታደራዊ አገዛዝ ስር መወደቁ ይፋ ከሆነበት ቀን ጀምሮ በስም የሚታወቁ ከ70 በላይ ሰዎች በትግራይ ሕዝብ ነጻአውጪ ግምባር (ህወሃት) ገዳይና አልሞ ተኳሾች የከበረው ህይወታቸው ተቀጥፏል። ህጻናት፣ አዛውንት፣ ወጣቶች፣ ሴቶች በግፍ ተገድለዋል፤ በጅምላ ታስረዋል። እስር ቤት አልበቃ ብሎ ትምህርት ቤቶች ማጎሪያ ሆነዋል። በየአቅጣጫው የሚወጡ መረጃዎች እንደሚያረጋግጡት የታፈኑ፣ ተረሽነው በጅምላ የተቀበሩ፣ የተሰወሩ፣ ቤተሰብ እርም ያላወጣላቸው በርካታ ናቸው። ከሁሉም በላይ በሽሽት ዱር የገቡ ቁጥር ስፍር እንደሌላቸው ለቪኦኤና ለኢሳት መረጃ ከሚሰጡ ለማረጋገጥ ተችሏል። የዝግጅት ክፍላችንም በርካታ መረጃዎች ደርሰውታል።

በኦጋዴን ዙሪያው ተዘግቶ እንደተካሄደው ጭፍጨፋ፣ ዛሬም ዓለም መረጃ እንዳይደርሰው ኢንተርኔትና ስልክ ተጠርቅሞ አማራ ክልል በጅምላ የሚካሄደው ጭፍጨፋ ምን ያህል የከፋ እንደሆነ ወደ ስፍራው ሲጓጓዙ ከነበሩት መሳሪያዎች አይነትና ክብደት ለመረዳት እንደሚቻል ብዙዎች እያነቡ ነው የሚገልጹት። ባዶ እጃቸውን ተቃውሞ የሚያሰሙ ወገኖችን ለጥያቄያቸው ህጋዊ መልስ ከመስጠት ይልቅ “ህልሜ እስኪፈጸም እኔ ካልገዛኋችሁ እትብታችሁ በተቀበረበት ቦታም ቢሆን የመኖር ተስፋ የላችሁም” በሚል ጸጉረ ልውጥ ቅጥር ነፍሰ ገዳዮች ተመድበውላቸው በጅምላ እየተፈጁ መሆኑንን ሰለባዎች በሃዘን እየገለጹ ነው። ባገራቸው ምድር እየተለቀሙ በውል በማይታወቅ ማጎሪያ እየታጎሩ ነው።

ተራራ ያንቀጠቀጠ” እየተባለ ያለገድሉ ታሪክ ሲጻፍለት፣ ከበሮ ሲደለቅለት የኖረው ህወሃት አስቀድሞ በጋዜጠኛ ሲንቀጠቀጥ ኖሮ አሁን ደግሞ በሰላማዊ ሰልፈኛ ከተንቀጠቀጠ ወዲህ በረሃ የተከተበው የቀድሞው አውሬ ባህርዩ በይፋ እየታየ መጥቷል፡፡ የረሃብተኛ እህልን በጠራራ ጸሃይ በመዝረፍ የራሱን ወገን በጥይትና በረሃብ የቆላው ህወሃት፣ “ነጻ አወጣሃለሁ” የሚለውን ህዝብ በተለያዩ ስልታዊ መንገዶች በመጨፍጨፍ ሥልጣን የጨበጠው “የባለ ራዕዩ” ህወሃት፣ ከተማ መሃል ታክሲ ውስጥ ቦምብ በመጥመድ የንጹሃን ደም ያፈሰሰው አሸባሪው ህወሃት፣ … አልገዛም ለውን ሕዝብ እየጨፈጨፈና እያፈነ ባለበት በአሁኑ ሰዓት አዲስና አስደንጋጭ ዜና መስማት ተጀምሯል። እስር ቤቶች እየጋዩ መሆናቸው!!

ቀደም ሲል አምቦ እስር ቤት ጋየ። የጉዳቱ መጠን በቅጡ ሳይታወቅ ተድበስብሶ ታለፈ። ከዚያም ጎንደር አንገረብ እስር ቤት ነደደ ተባለ። እዚያም የደረሰው ጉዳትና የጉዳቱ መጠን በቅጡ ሳይነግር ተሸፋፍኗል፤ አሁን ደግሞ “ቂሊንጦ እስር ቤት ጋይቷል። ቃጠሎው እነ በቀለ ገርባን ጨምሮ  ታዋቂ የፖለቲካ አመራሮች፣ የሃይማኖት መሪዎች፣ የመብት ተከራካሪዎችና የስርዓቱ ሰለባዎች ስለሚገኙ ዜናው ህወሃት ለገጠመው ቀውስ እንደ ነዳጅ ሆነ። ቃጠሎው ይፋ መሆኑን ተከትሎ ቅድሚያ አቶ ጃዋር መሐመድ ይህንን አስደንጋጭ ማሳሰቢያ በፌስቡክ ገጹ ይፋ አደረገ።

ወያኔ በቀለ ገርባ እና ሌሎቹ አመረሮች በህይወት መኖራቸውን በሚቀጥሉት 3 ሰዓታት ውስጥ ተጨባጭ ማረጋገጫ ካልሰጠ የሚቀጥሉት እርምጃዎች ይወሰዳሉ

1) በሁሉም ደረጃ ያሉ እስር ቤቶች ይወድማሉ

2) ማንኛውም የወያኔ ንብረት ይወድማል

3) መንግዶች በሁሉም አቅጣጫ እና ሰፈር ይዘጋሉ (ኢንተርኔት ሊዘጉ ስለሚችሉ ይህን መልክት በአስቸኳይ አስተላልፉ) #oromoProtests

የኢህአዴግ አንደበት የሆነው ፋና ብሮድካስቲንግ አንድ ሰው መሞቱንና ስድስት መቁሰላቸውን የፌደራል ማረሚያ ቤቶች አስተዳደር የህዝብ ግንኙነት ዳይሬክቶሬት ጠቅሶ ዘገበ። በቴሌቪዥን ስርጭትም ተመሳሳይ ዜና ቀርቦ ዝርዝሩ ሲጣራ እንደሚቀርብ ተጠቆመ። ዜናው ሽባ በመሆኑና ጥርት ያለ መረጃ የሚሰጥ ሆኖ ባለመገኘቱ አሁንም ጃዋር እንዲህ ሲል በድጋሚ በፌስቡክ ገጹ ማስጠንቀቂያ ሰጠ።

“በቂሊንጦ እስርቤት የተኩስና እሳት አደጋ መኖሩ ለህዝብ ጆሮ ከደረሰ 12 ሰአታት አለፉት። መንግስት ቢያንስ የፖሊቲካ መሪዎቹን ደህንነት እንዲሳውቅ ከተጠየቀ ሶስት ሰዓታት አለፉ። እስካሁን መሪዎቹ ደህና ስለመሆናቸው ለቤተሰቦቻቸው፤ ለጠበቆቻቸውም ሆነ ለህዝብ ምንም አልተነገረም። ይህ ዝምታ በአመራሩ ላይ የከፋ አደጋ ለመድረሱ አመላካች ነው። አዲስ ፎርቹን ቢያንስ 20 ሰዎች መገደላቸውን ዘግቧል። መሪዎቻችን ከነዚህ የአረመኒያዊ ጭፍጨፋው ሰለባ ላለመሆናቸው ምንም ማረጋገጫ የለም። እናም ህዝባችን በቻለው መንገድ ሁሉ እርምጃ መውሰድ መብቱም ግዴታውም ነው!”

“ንገሩን!! የት እንዳሉና በምን ሁኔታ ላይ እንደሚገኝ ንገሩን። ወይም ሞተው ከሆነ አስከሬናቸውን ስጡን” ሲሉ የአቶ በቀለ ገርባ ባለቤት ወ/ሮ ሃና በስልክ አግኝቷቸው እንደነገሩት የገለጸው ኤሊያስ ገብሩ ጎዳና ወ/ሮ ሃና ስለባለቤታቸው የተናገሩትን ጨምሮ ዘግቦ ነበር፡፡ “ከበቀለ ጋር ባሳለፍነው ሐሙስ ቂሊንጦ ተገናኝተን በሰላም ተነጋገረን ነበር። ትናንት ለጥየቃ መግባት አልቻልኩም። ዛሬ ልጃችን ቦንቱ ሄዳ ነበር። ረፋድ ላይ በቂሊንጦ በተነሳው ቃጠሎና ተኩስ ምክንያት ደውላለኝ ተነጋግረናል። ቀኑን ሙሉ በአካባቢው ብትገኝም አባቷን መጠየቅ ሳትችል ወደቤት ተመልሳለች። በቀለም ሆነ ሌሎች በቂሊንጦ እስር ቤት ያሉ ወገኖቻችን በምን ሁኔታ ላይ እንዳሉ ማወቅ አልቻልንም። ነገ እኔና ልጄ ቂሊንጦ እንሄዳለን …” ሲሉ ከቃጠሎው በኋላ ስሜታቸውን ገልጸዋል።

በተለያዩ ወገኖች የሚወጡ መረጃዎች እንደሚያስረዱት የቂሊንጦ ማጎሪያ ቃጠሎ ከመታየቱ በፊት ተኩስ ይሰማ ነበር። በእስረኞች በኩል እስርቤቱን ደርምሶ ለመወጣት ሙከራ መደረጉን ህወሃት ደጋፊዎች ይናግራሉ፡፡ ከቃጠሎው በኋላ 22 የሚጠጉ ሰዎች መሞታቸውና በውል የማይታወቁ ክፉኛ ተጎድተው ጦር ሃይሎች ሆስፒታል መግባታቸው ተሰምቷል። ህይወታቸው አለፈ የተባሉትን 22 ሰዎች ጳውሎስ ሆስፒታል እንደተረከበ የሚግልጹ ወገኖች “አስከሬኖቹ በመከላከያ ወታደሮች ታጅበው ነበር” ብለዋል። እሁድ ማለዳው ላይ በማኅበራዊ ድረገጾች የተሰራጨ መረጃ የሟቾች ቁጥር 50 መድረሱ ሲገልጽdaniel berhane በይፋ ባይረጋገጥም አቶ በቀለ ገርባ በህይወት መኖራቸው ተነግሯል፡፡ የሟቾች ማንነት እስከአሁን ለማወቅ አልተቻለም፡፡

አሳዛኙ የእስርቤት ቃጠሎ በተሰማ ጊዜ ዳንኤል ብርሃኔ የሚባል የህወሃት ደጋፊ ያለ እረፍት በፌስቡክ ገጹ በሚለቀው መረጃ ላይ በቃጠሎው ሚኒስትር ዴኤታዎች እንዳሉበት ገልጾ ነበር፡፡ “ስም ዝርዝ(ራቸውን) እንደአስፈላጊነቱ በይፋ እንለቃለን” በማለት በራሱ ገጽ ላይ እንደብዙ ሰው ተናገሯል፡፡ የህዝብ አልገዛም ባይነት ያስጨነቀው ህወሃት ባንድ ወር ሁሉን እናስተካክላለን በሚል “ተላላኪ፣ የውስጥ አርበኛ፣ አንጃ፣ …” በማለት ምሳ ሊያደርጋቸው ያሰበውን ተረኞች ዳንኤል ጌቶቹን ሳያስፈቅድ የፌስቡክ ቁርስ አድርጓቸዋል፡፡ መረጃውን እንደለቀቀ አንድ አገር ውስጥ የሚገኝ ታማኝ የመስመር ጋዜጠኛ “አፈርኩብህ” ሲል ጉዳዩ በምርመራ ሳይረጋገጥ የሚኒስትር ዴኤታዎችን ስም ከቃጠሎው ጋር ወንጅሎ ማቅረቡ አግባብ እንዳልሆነ አስተያየት ከሰነዘረበት በኋላ ቀለብ ሰፋሪ ጌቶቹ በሰጡት ቀጭን ትዕዛዝ መረጃውን ከፌስቡክ ገጹ ላይ አንስቶታል፡፡ “በጋዜጠኛነት” ታፔላ ፌስቡክ ላይ የሚክለፈለፍ አንድ ተራ ግለሰብ በአገር አስተዳደር ላይ የተሰየሙ ከፍተኛ ባለሥልጣናትን ባልፈጸሙት ወንጀል ስማቸውን ማጥፋቱ አግባብነት የለውም የሚሉ አስተያየት ሰጪዎች በሚኒስትር ደኤታነት የተቀመጡት ባለሥልጣናት ማስረጃውን በመያዝ ጉዳዩን ወደ ሕግ መውሰድ ይገባቸዋል በማለት ይመክራሉ፡፡

Received on Sun Sep 04 2016 - 04:42:20 EDT

Dehai Admin
© Copyright DEHAI-Eritrea OnLine, 1993-2013
All rights reserved