Goolgule.com: የመለስ “ሌጋሲ” የመጨረሻው ዙር የመጀመሪያ ክፍል?

From: Berhane Habtemariam <Berhane.Habtemariam_at_gmx.de_at_dehai.org>
Date: Thu, 26 May 2016 22:38:34 +0200

የመለስ “ሌጋሲ” የመጨረሻው ዙር የመጀመሪያ ክፍል?

የኢሳያስ ጉዳይ “ተስቦ” እንዳያስነሳ ተፈርቷ!
isayas
 

ሰሞኑን የተሰማው ዜና በህወሃት መንደር የሥርዓት መናጋትና የፖለቲካው ችግር ነጸብራቅ እንደሆነ ብዙዎች ይስማማሉ። “ይህ ችግር እንደ ተስቦ ይዛመታል፤ ሲዛመት መቆሚያ አይኖረውም” የሚሉም አሉ። ሲያክሉም “ተስቦው ወደ መበላላት ሊያመራ ይችላል። ይህ ሊሆን ግድ ካለ ደግሞ እሽቅድድም ይጀመራል። እሽቅድድም ሲኖር ላለመቀደም የፈሪ ዱላ አይነት ጨዋታ ይነሳል። የፈሪ ዱላ ክፉ ነው” በሌላ በኩል ደግሞ ሁሉንም ወገኖች አስተሳሰብ የሚያጣጥሉ አልታጡም።

ይህ አስተያየት የተሰጠው ከሁለት ሳምንት በፊት አብረዋቸው ከሚሰሩት ባለቤታቸው ጋር ከሃላፊነታቸው ተነሱ የተባሉት የመረጃና የደህንነት ምክትል ዋና ዳይሬክተር አቶ ኢሳያስ ወልደጊዮርጊስ ዜና ተከትሎ ነው። አቶ ኢሳያስ የደህንነቱ “መለስ” በሚል ስያሜ ይጠሩ ስለነበር ዜናው በህወሃትም ሆነ ህወሃት “መንግስት” የመሆን አጋጣሚ ሲመቻችለት ባቋቋመው ኢህአዴግ ውስጥ መደናበር አስከትሏል። በመለስ ራዕይ፣ ውርስ፣ አጽምና መንፈስ የሚምለው አዲሱ የህወሃት ሃይል የመለስን ቡድን ቀስ በቀስ  መብላቱ “ለምን ይሆን?” የሚለው ጥያቄ ዜናውን ሚዛን ላይ ያወጣዋል።

Kinfe+Gebremedhin

ክንፈ ገብረመድህን

አቶ ኢሳያስ ታጋይ የነበሩ፣ የሟቹ የደህንነት ሚኒስትር አቶ ክንፈ ገብረመድህን ምክትል ሆነው ያገለገሉ እንደሆኑ በገሃድ የሚታወቅ ነው። አቶ ክንፈ በድንገት ሲገደሉ ግን ከምክትልነታቸው ከፍ ብለው እሳቸውን እንዲተኩ አልተደረገም። ይልቁኑም የሆነው አቶ ጌታቸው አሰፋን በላያቸው ማስቀመጥ ነበር። ለምን? ይህ ጥያቄ እስካሁን ጥርት ያለ መረጃ አልተሰጠበትም። ለህወሃት ሲያገለግሉ የነበሩና ስርዓቱን የከዱም ቢሆን በቂ ማብራሪያ ያላቀረቡበት ድንግዝግዝ ጉዳይ ነው።

አቶ ኢሳያስ “ተሰው” የሚባሉት የአቶ መለስ ቀኝ እጅ፣ የልብ ትርታ፣ የአየር ቧንቧቸው መሆናቸው የሚታወቀው እስከ መንደር ባለው መዋቅርና በየድራፍት ቤት ጭምር ነው። ታዲያ አቶ ኢሳያስ የመለስ ታማኝ ከሆኑ “ከመለስ ራዕይና ውርስ አምልኮ ፈቀቅ አንልም” በማለት በሚምሉት “ውርስ ጠባቂና አስጠባቂ” አዲስ አመራሮች እንዴት አመኔታን አጡ? የሚል ጥያቄ ማስነሳቱ አይቀርም። ህወሃት በተሰነጠቀበት የህንፍሽፍሽ ዘመን የአቶ መለስ ጥፍር ይዘው ካዳኗቸው ጋር በማበር ቀዳሚ ናቸው ከሚባሉት አቶ ደብረጽዮን ገብረሚካኤል ያልተናነሰ ሚና የነበራቸው አቶ ኢሳያስ ዛሬ ምን ተገኘባቸውና በመለስ ወዳጆች ይህ ወሳኔ ተላለፈባቸው? የኤርትራ ደም ስላለባቸው? እነ በረከት ስለሟሙ? ወይስ በሌጋሲ የሚማልበት ስልታዊ ጉዞ ማበቂያ? ወይስ የመለስ ውርስ የጥሎ ማለፍ ድራማ ተቋጨ? ወይስ ዳግም ህንፍሽፍሽ ሊመጣ? ምንም ይሁን ምን ግን ውሳኔው ቀውስን አመላካች ከመሆን እንደማይዘል በርካቶችን ያስማማል።

ኢሳያስን ማን አባረራቸው?

ግንቦት 16፤ 2008ዓም (ሜይ 24/2016) ኢሣት “ሰበር” ሲል አቶ ኢሳያስና ባለቤታቸው በተመሳሳይ ከሃላፊነታቸው እንደተነሱ ይፋ ማድረጉን ተከትሎ ጎልጉል በራሱ መስመር ለማጣራት እንደሞከረው አቶ ኢሳያስ እንዲሰናበቱ የተወሰነው በህወሃት ሥራ አስፈጻሚ ውሳኔ ነው። ውሳኔው ሲወሰን ተሳታፊ ከነበሩት የስራ አስፈጻሚዎች መካከል አለቃቸው አቶ ጌታቸው አንዱ በመሆናቸው አቶ ኢሳያስን ለማሰናበት ውክልናውን የወሰዱት እዚያው ስብሰባው ላይ ስለመሆኑ መረጃ ያላቸው አመልክተዋል። አቶ ኢሳያስ የህወሃት ማዕከላዊ ኮሚቴ ቢሆኑም ራሳቸውን ማዳን አልቻሉም። (ዘጠኙ የህወሃት ሥራ አስፈጻሚዎች፤ አባይ ወልዱ፤ ደብረፅዮን ገ/ሚካኤል፤ ቴድሮስ ኣድሓኖም፤ በየነ ምክሩ፤ አዜብ መስፍን፤ አለም ገ/ዋህድ፤ ጌታቸው አሰፋ፤ አዲስአለም ባሌማ፤ ፈትለወርቅ ገ/ሄር ናቸው፡፡ ከ144 የኢህአዴግ ምክርቤት አባላት ውስጥ ከህወሃት ከሚወከሉት 36 ወያኔዎች መካከል ኢሳያስ ወልደጊዮርጊስ አንዱ ናቸው)

debretsion-and-abay

ደብረጽዮንና አባይ ወልዱ

አቶ ኢሳያስ ቢሯቸው በደህንነትና መረጃ ህንጻ ሳይሆን በውጪ ጉዳይ ሚኒስትር ውስጥ እንደሆነ የጠቆሙት ክፍሎች እንዳሉት አቶ ኢሳያስ የስንብት ደብዳቤ የደረሳቸው ከ13 ቀን በፊት ነው። ደብዳቤው ከደረሳቸው በኋላ ባይታሰሩም በጥብቅ ቁጥጥር ስር መሆናቸውን አመልክተዋል። ኢሣት እንዳለው አቶ ሃይለማርያም ውሳኔ ያልሰጡበት ይህ ከፍተኛ የተባለ የፖለቲካ ውሳኔ ይህ ዜና እስከተጠናከረ ድረስ ከጉዳዩ ባለቤቶች ይፋ መግለጫ አልተሰጠበትም። ለገዢው ኢህአዴግ ቅርብ የሆኑና የሚደጎሙ የስም “ነጻ” ጋዜጦችም ዜና አላደረጉትም።

ከውህዳኑ ጋር ያበሩ መስለው ከመሰንጠቁ አደጋ በኋላ የመለስ አጋር ሆነው በሁለት ቢላ ሲጫወቱ እንደነበር ይፍ የወጣባቸው አባይ ጸሀዬና “የስለላው ድብቅ ማሽን” የሚባሉት ደብረጽዮን ገ/ሚካኤል ኢሳያስ ወልደጊዮርጊስን ከመታደግ ይልቅ ሰይፍ እንዲመዘዝባቸው በተወሰነው ውሳኔ ጀርባ ዋና ተዋናይ እንደሆኑ ለጉዳዩ ቅርበት ያላቸው ክፍሎች ይጠቁማሉ።

የመባረሩ ጭምጭምታና መነሻ

አቶ ኢሳያስ በዚህ መልኩ ከሃላፊነታቸው ይነሳሉ በሎ ማሰብ ከባድ እንደሆነ በዙዎች ይስማማሉ። አቶ መለስ በህይወት በነበሩበት ዘመን ዋና አለቃቸው አቶ ጌታቸውን የሸራተን ምድብተኛ አድርገው ሲፈልጡና ሲቆርጡ፣ ከፍተኛ ኦፕሬሽኖችን ሲመሩና ኤርትራን በስምንት የብሔር ክልሎች ሸንሽኖ ለማስተዳደር አቶ መለስ ላቀዱት እቅድም ተግባራዊነት በግንባር ቀደም ሃላፊነት ወስደው ይሰሩ የነበሩት አቶ ኢሳያስ ዛሬ ሰይፍ የተመዘዘባቸው ምክንያት በውል መጠቆም ቢያዳገትም የተለያዩ መላምቶች እየተሰጡ ነው።

yhannes gmeskel

ዮሀንስ ገብረመስቀል ተስፋማርያም

በደቡብ ሱዳን የሰላም አስከባሪ አዛዥ ሆነው በጁን 17/ 2014 ተሹመው የነበሩት  ሌፍተናን ጀኔራል ዮሀንስ ገብረመስቀል ተስፋማርያም እና አቶ ኢሳያስ ስምምነት እንዳልነበራቸው የሚያውቁ አሉ። ወደ ደቡበ ሱዳን ከመዛወራቸው በፊት የመከላከያ ደህንነት ሃላፊ የነበሩት እኚሁ መኮንን በቀርቡ ከደቡብ ሱዳን ሥራቸው ተመልሰዋል። ለጉዳዩ ቅርብ የሆኑ እንደሚሉት ጄኔራሉ የሚመለሱት የቀደሞው ሃላፊነታቸው ላይ ነው። እንደ እነዚህ ክፍሎች አባባል ኢሳያስና ጄኔራሉ አብረው ሊሰሩ ስለማይችሉ ውሳኔው ተወስኗል።

ከዚህ ጋር ተያያዥነት ይኑረው አይኑረው ባይታወቅም  በጋምቤላ የተፈጸመውን ግድያ አስመልክቶ በአፕሪል 20/ 2016 ሰንደቅ ጋዜጣ “የገዢው ፓርቲ የፖለቲካ አመራር ግራ አጋቢ ገፅታዎች” በሚል ርዕስ “…የፖለቲካ አመራሩ መከላከያ ሚኒስቴርን እና የደህንነት መስሪያቤትን በበላይነት የሚመራ አካል መሆኑ በሕገመንግስት የተቀመጠ ነው። ከዚህ አንፃር የመሰለኝ ምላሽ የሚያቀርበው የፖለቲካ አመራሩ ከመከላከያ ሚኒስቴር እና ከደህንነት መስሪያቤት የሚደርሰውን መረጃ የመተንተን እና የፖለቲካ አመራር የመስጠት ውስንነት አለበት፤ ወይም ለፖለቲካ አመራሩ ከመከላከያ እና ከደህንነት መስራቤቶች የሚደርሰው መረጃ ከአካባቢው ኩነቶች ጋር የማይዛመድ ነው፤ ወይም መከላከያ ሚኒስቴር እና ደህንነት መስሪያቤት ተናበው አይሰሩም፤ ወይም የፖለቲካ አመራሩ መከላከያ ሚኒስቴርን ከደህንነት መስሪያቤት ወይም ደህንነት መስሪያቤትን ከመከላከያ ሚኒስቴር አስበልጦ የማመን ሰልፍ ውስጥ ተዘፍቆም ሊሆን ይችላል” በማለት “ሁንኛ” ከሚባሉት አምደኞቹ በአንዱ በኩል ጠቋሚ ሊባል የሚችል መረጃ አውጥቶ ነበር፡፡

በሌላም በኩል የሚነሳው ዋና ጉዳይ አቶ ኢሳያስ ባገሪቱ የተፈጸሙትን ከፍተኛ ሙስናዎች፣ ራሱ ህወሃት ሆን ብሎ ባለስልጣናትን “ለማበስበስ” ሙስና ውስጥ የዘፈቃቸውን ባለስልጣናት መረጃ ጠንቅቀው ስለሚያውቁ፣ ህወሃትን በስለላው ውስጥ በሚያግዙ ባለሃብቶች አማካይነት ባለስልጣናትን በማበስበሱ ጉዳይ ዋና መሪ በመሆናቸው ሰለባ ሆነዋል የሚሉ አሉ። የሳቸው ከሙስና ነጻ መሆን እንዳለ ለጊዜው በይደር የሚቆይ ቢሆንም፣ አሁን በከፍተኛና ነባር የህወሃት አመራሮች ዙሪያ የሚሽከረከረውን የሙስና ዘመቻ በስጋት የሚከታተሉ የህወሃት ሰዎች አቶ ኢሳያስን ቀድመዋቸዋል የሚል ሃሳብም ይነሳል። የፌደራል የስነ ምግባርና ጸረ ሙስና ኮሚሽን እያለ ታክስ ፎርስ ተቋቁሞ ሙሰኞች ላይ ርምጃ እንዲወሰድ አቶ ሃይለማሪያም ሲያስወስኑ አቶ ኢሳያስ የዚሁ ታክስ ፎርስ መሪ እንዲሆኑ ታጭተው እንደነበር የሚያውቁ ይናገራሉ። አቅም አልባው ሃይለማርያም ደሳለኝ ባሰቡት መልኩ ታክስ ፎርሱ ስራውን ሳይጀምር የአቶ ኢሳያስ ከሃላፊነት መነሳት ጉዳዩን ውስብስብ እንዳደረገባቸውና ለጊዜው አስትያየት ለመስጠት እንደሚቸግራቸው የሚገልጹ ክፍሎች “መጨረሻውን ማየት የግድ ነው” ሲሉ ይደመጣሉ። አሁንም ሰንደቅ ይህንን በተመሳሳይ ርዕስ ስርያስነብባል፤

“… ሌላ ገጽታም ከወሰድነው፣ ገዢው ፓርቲ አሁን ለተፈጠረው የቀውስ አዙሪት የመልካም አስተዳደር ችግር መሆኑን በተደጋጋሚ እየገለጸ ነው የሚገኘው። በተለይ ከአብይ ሙስና ‘Grand Corruption’ ጋር በተያያዘ ለሕልውናውም አስጊ መሆኑን መገንዘቡን ከመናገር አልተቆጠበም። ከፍተኛ የፖለቲካ አመራሮች አብይ ሙስናዎች መፈፀማቸውን መረጃ በመሰብሰብና በመተንተን የደህንነት መስሪያቤቱ ከፍተኛ ድርሻ እንደነበረው ይታወቃል። በዚህ የደህንነት ተቋም የተሰበሰቡ መረጃዎች የሚያሰጋቸው የፖለቲካ አመራሮች በተለያዩ ቦታዎች ቀውስ በመፍጠር የተቋሙ አመራሮችን በመወንጀል ከኃላፊነታቸው ለማስነሳት የሚሰሩትም ደባ ሊሆን ይችላል። ወይም በተለያዩ ቦታዎች ፖለቲካዊ ቀውሶች በመፍጠር ከመልካም አስተዳደር አጀንዳ በፊት የሀገሪቷ ደህንነት መቅደም አለበት የሚል የጊዜ መግዣ አጀንዳ ለማስቀመጥ የሚደረግ መገላበጥም ሊሆን ይችላል” ይላል፤ ይህንን አስፈንጣሪ በመጫን ሙሉ ዘገባውን ማንበብ ይቻላል። ስለ ሰንደቅ ጋዜጣ ተፈጥሮና ጸሃፍት ማንነት የሚያውቁ ይህንን መረጃ አያጣጥሉትም።

ሰንሰለቱና ተስቦው

የኢሳያስ ወልደጊዮርጊስን ከሃላፊነት መነሳት የሰሙ በቀጥታ የጠየቁት “ሰንሰለቱስ?” በማለት ነው። ሃላፊው በቀጥታ ከመለስ ጋር ግንኙነት ፈጥረው ሲሰሩ በነበረበት ወቅት የዘረጉት፣ እሳቸው በቀጥታ መለስን እንደሚያገኙ፣ እሳቸውን በቀጥታ የሚገናኙና በከፍተኛ ኦፕሬሽኖች ውስጥ ተዋናይ የነበሩና አሁንም በሳቸው መስመር የሚሰሩ ስለመኖራቸው ጥርጥር የለም። በሲቪል ተቋማት፣ በመከላከያ፣ በፖሊስ፣ በራሱ በደህነነት፣ በክልል የጸጥታ ዘርፍ፣ በክልል አስተዳደርና ነጋዴዎች፣ በተለያዩ ተቋማት፣ እሳቸው መስመር ውስጥ የተሰገሰጉ የስራው አካላት እጣ ፈንታ ምን ሊሆን ይችላል? የሚለው ጉዳይ የዜናው ሌላው አስኳል ጉዳይ ነው።tplf-vs-eplf

እንግዲህ ይህንን ሰንሰለት በተመለከተ አስተያየት የተጠየቁ “ተስቦ ነው” ሲሉ ጉዳዩን ከወረርሺኝ ጋር ያያዙት። “ተስቦው ወደ መበላላት ሊያመራ ይችላል። ይህ ሊሆን ግድ ካለ ደግሞ እሽቅድድም ይጀመራል። እሽቅድድም ሲኖር ላለመቀደም የፈሪ ዱላ አይነት ጨዋታ ይነሳል። የፈሪ ዱላ ደግሞ አመታተሙም ሆነ የምቱ ኃይል እጅግ ክፉ ነው” ይላሉ፡፡

ሰንሰለቱ ወስጥ ያሉትን ጉዳዩ እያደር እንደ ተስቦ ይነካቸዋል። ስለዚህ ራሳቸውን ለመከላከል ዝግጅት ያደርጋሉ። ቀጣይ ርምጃዎች ሚስጥር ሊሆኑ የሚችሉበት አጋጣሚ እጅግ የሰለለ በመሆኑ ራስን የመከላከል ርምጃ በተለያዩ ደረጃዎች ሊከሰት እንደሚችል የጠቆሙት ክፍሎች “ይህ ሊሆን የሚችለው ግን አቶ ኢሳያስ የተነሱበት ጉዳይ ከደህንነቱ ስራ ጋር በተያያዘ በሚያውቁት ከፍተኛ ምሥጢር መጠን ወንፊት ሆነው ተገኝተው ከሆነ ወይም ህወሃት ውስጥ ተከስቷል በሚባለው ሁለት ጎራዎች ውስጥ ነባር አመራሩን ያባረረውን አዲሱን ሃይል ከድተው ከሆነ ብቻ ነው”፡፡ ህወሃት ውስጥ ነባር አመራሮች ዳግም ህወሃትን የመቆጣጠር ሙከራ ማድረጋቸውና ሳይሳካልቸው በእነ ደብረጽዮን ቡድን መሸነፋቸው አይዘነጋም።

“አዲስ ነገር የለም”

የአቶ ኢሳያስን ከሃላፊነት መነሳት “አዲስ ነገር አይደለም” የሚሉ ወገኖች በበኩላቸው ጉዳዩ መተካካት ከሆነስ ሲሉ ይከራከራሉ። ጉዳዩ መለስ እንዳሉት መተካካት ከሆነ ልዩነቱ አዲሱ አመራር ርምጃውን መውሰዱ ዜናውን ከባድ ካላደረገው በስተቀር አያስገርምም። ይህንን ወሳኔ አቶ መለስmelesna isayasበህይወት እያሉ አድርገውት ቢሆን ኖሮ ዜና እንደማይሆን የጠቆሙት ክፍሎች “ዜናው አሁን ገዝፎ የወጣው ህወሃት አንድ መሪ ስለሌለው ነው” ባይ ናቸው። እነዚሁ ክፍሎች ህወሃት የሻዕቢያ ውልድ መሆኑን ከዚህ ጋር በማገናኘት ይህ የኢሳያስ ከሃላፊነት መነሳት ሆን ተብሎ ለሕዝብ “የቤት ሥራ” ከመስጠት ውጪ አንዳች ፋይዳ አይኖረውም በማለት ይሟገታሉ፡፡

እነዚህ ክፍሎች ይህንን ቢሉም ግን ጉዳዩ እያደር የሚተለተል፣ የሚተሳሰብና የሚሰፋ ስለመሆኑ አይጠራጠሩም። ይፋ አያድርጉት እንጂ ወይዘሮ አዜብ ዙሪያ ያሉትን ጨምሮ ሌሎች የደህንነት የመስመር ሃላፊዎች ተመሳሳይ ርምጃ እንደተወሰደባቸው ፍንጭ ይሰጣሉ። ጉዳዩ በዚህ መስመር ከቀጠለ “የመለስ ሌጋሲ” የተባለው ተከታታይ “ድራማ” የመጨረሻው ዙር የመጀመሪያ ክፍል ተብሎ ሊወሰድ ይችላል፡፡

Received on Thu May 26 2016 - 16:38:36 EDT

Dehai Admin
© Copyright DEHAI-Eritrea OnLine, 1993-2013
All rights reserved