ኤርትራዊ-አሜሪካዊ መብ ክፍለዝጊ በብራዚል ኦሊምፒክ የማራቶን ቡድን ሊመራ ነው

From: Semere Asmelash <semereasmelash_at_ymail.com_at_dehai.org>
Date: Mon, 11 Apr 2016 17:14:52 +0000 (UTC)

http://amharic.voanews.com/a/meb-kiflezghi-to-lead-a-marathon-group-in-rio-dejaneiro-eritrea-america-us/3279711.html

ኤርትራዊ-አሜሪካዊ መብ ክፍለዝጊ በብራዚል ኦሊምፒክ የማራቶን ቡድን ሊመራ ነው

ሚያዚያ 11, 2016 ሔኖክ ሰማእግዜር

መብራህቶም ክፍለዝጊን አሜሪካኑ እያቆላመጡ ነው የሚጠሩት -- መብ እያሉ። ኤርትራ ሳለ የነበረውን የኑሮ ሩጫ ብንቀንስ ስራዬ በሎ የሮጠው ርቀት ዓለምን ከአራት ጊዜ በላይ የሚያዞር ነው፤ ሩጫው አሁንም ቀጥሏል።

ዋሽንግተን ዲሲ — በመጭው ነሐሴ ወር በሪዮ ዴ ጀኔሮ በሚካሄዱት የኦሊምፒክ ጨዋታዎች የዩናይትድ ስቴይትስን የማራቶን ቡድን የሚመራው የ41 ዓመቱ ኤርትራዊ-አሜሪካዊ መብ ክፍለዝጊ ነው።

በሳን ዲያጎ ካሊፎርኒያ ልምምድ በማድረግ ላይ ሳለ የአሜሪካ ድምጿ ኤልዛቤት ሊ አነጋግራዋለች። ለመሆኑ ከኤርትራዊ ስደተኝነት ወደ ዩናይትድ ስቴይትስ ዜጋነትና፤ ምናልባትም የአዲሲቱ ሀገሩ የተከበረና ብርቱ አትሌት እንዴት ሊሆን ቻለ?

መብራህቶም ክፍለዝጊን አሜሪካኑ እያቆላመጡ ነው የሚጠሩት -- መብ እያሉ። ኤርትራ ሳለ የነበረውን የኑሮ ሩጫ ብንቀንስ ስራዬ በሎ የሮጠው ርቀት ዓለምን ከአራት ጊዜ በላይ የሚያዞር ነው፤ ሩጫው አሁንም ቀጥሏል።

መብ ክፍለዝጊ ከዚህ በፊት በሶስት የኦሊምፒክ ውድድሮች ተሳትፎ፤ በ2004 ዓ.ም. በአቲንስ በተካሄደው ውድድር የብር ሜዳልያ ተሸላሚ ሆኗል። መብ በሪዮ ኦሊምፒክስ ሜዳልያ ካገኘ፤ በአሜሪካ ታሪክ በእድሜ ትልቁ የኦሊምፒክ ማራቶን ሯጭ ይሆናል። አሜሪካዊያን ቴዲ አፍሮ የላቸውም እንጂ እንዲህ ብለው ያዜሙለት ነበር። መብ ክፍለዝጊ ሩጫ የጀመረው የመጀመሪያ ደረጃ ተማሪ ቤት ሳለ እንደሆነ ይናገራል።

"አንድ ማይል በአምስት ደቂቃ ከ20 ማይክሮሰከድ ገደማ ሮጥኩና በትምህርቴ A አገኘሁ። አንድ ቲሸርትና “ጎበዝ በርታ!” የሚሉ ምስጋናዎች ጎረፉልኝ። በቃ የኔ አይናፋር የነበርኩት ልጅ፤ ጥላየ ተገለጠለኝ።' ብሏል።

በወቅቱ የትውልድ ሀገሩ ኤርትራ በጦርነት ላይ ስለነበረች፤ እንዲህ አይነት የሩጫ ድል ህይወቱን የመለወጥ እድሉ አነስተኛ እንደሆነ ይናገራል።

"ትምህርት ቤት የመሔድ እድሎች ጠባብ ነበሩ። በመላ ሀገሪቱ የሚታየው ወታደሮች ሲንቀሳቀሱ ነበር። የተቀበሩ ፈንጂዎች ሜዳ ተራራውን ሞልተው ስለነበር ኑሯችን የከፋ፤ በተለይ ደግሞ ልጆች ለማሳደግ አስቸጋሪ ነበር። በምርጫ ስላልሆነ በአንድ አካባቢ የምንወለደው፤ የኔ እጣ ይሄ ሆነ። ለዚህ ነው ቤተሰቤ ሀገር ለቆ የተሰደደው።" ይላል መብ።

በዩናይትድ ስቴይትስ በርካት እድሎች ቢኖሩም፤ ለመብና ቤተሰቡ ኑሮ ቀላል አልነበረም።

"ቋንቋው የተለየ በመሆኑ እራሴን ለመግለጽ እቸገር ነበር። ዝምተኛና ጭምት ያደርግሃል። የምታስበው ነገር ጠፍቶ ሳይሆን፤ ቃላት ያጥራሉ፤ እንዴት ልናገረው እያልክ ስታስብ፤ በቃ ሳይታወቅህ ለረጂም ጊዜ ጸጥታን መምረጥ ትጀምራለህ።"

የመብ ክፍለዝጊ አሰልጣኝ ሆነው ለ20 ዓመታት አብረው ሰርተዋል። የተዋወቁትም ላርሰን የዩኒቨርስቲ ኦፍ ካሊፎርንያ (University of California) የስፖርት አሰልጣኝ ሳሉ ነው። ለመብ ነጻ ሙሉ የትምህርት እድል የሰጡትም ላርሰን ናቸው። ምክንያታቸውን ሲያሰረዱ፤ መብ እጅግ ጽኑ ባህሪ ስለነበረው ነው ይላሉ።

"በጣም ልዩ ሰው ነው። ያደገበው አስቸጋሪ ሁኔታ ያበረታው ይመስለኛል። በዩናይትድ ስቴይትስ ደግሞ በርካታ ልጆች ባሉበት ቤት ስላደገ፤ በተለይ በሩጫው በየጊዜው ሲተጋ አንዳንድ የቤተሰቡ አባላትም መካከል ማጉረምረም ነበር። በየስፍራው እየተጓዘ ይሮጣል፤ ባገኘበት ዘመድም ጓደኛም እየፈልገ ያድራል። ባጭሩ ቤተሰቡን የሚገልጸው ጽኑ የሚል ቃል ነው።" ብለዋል።

አሰልጣን ላርሰን ስለ መብ ሲናገሩ፤ ጫናን የመሸከብ ብቃት ያለውና፤ ብርቱ ስለሆነ፤ ማራቶኖችን የሚያሸንፈው በዚህ ጽናቱ ነው ይላሉ።

"ከአምስት ዓመት በፊት የኒውዮርክ ማራቶን አሸንፏል የቦስተን ማራቶንን ደግሞ ከሁለት አመት በፊት በድል ተወጥቷል። እነዚህን ውድድሮች አሸንፎ፤ በተጨማሪ የኦሊምፒክ ሜዳልያ ያከለ ሯጭ የለንም።" ብለዋል።

መብራቱ የቦስተን ማራቶንን ያሸነፈው በውድድሩ ፍጻሜ መስመር ላይ አሸባሪዎች ጥቃት ባደረሱ በዓመቱ ነበር። የቦስተን ማራቶንን አሸንፎ የመጨረሻ መስመሩን ሲያቋርጥ የተሰማው ደስታ፤ ከኦሊምፒክ አሸናፊነቱም የላቀ ነበር።

"የሩጫ ሕይወቴ ታላቅ የደስታ ቀን ነበር። በዚች ዓለም በሩጫ ብርታትና ጽናት፤ ሌሎችን በበጎ መልኩ ሲያንጽ መመልከት ደስ ይላል።" ብሏል።

የመብ ክፍለዝጊ የቦስተን ድል ብዙ ክብረወሰኖችን ሰብሯል። አሜሪካዊ የቦስተን ማራቶንን ካሸነፈ 31ዓመታት ተቆጥረው ነበር። በሽብር ጥቃት በደረሰባት ቦስተን አሜሪካዊ ሲያሸንፍ “ቦስተን ስትሮንግ-- ቦስተን ብርቱ” የሚለውን የጽናት ቃል አጠናክሯል። መብ በሪዮ ኦሊምፒክስ ሌላ አዲስ ፈተና ከፊቱ አለ። ክብርም -- ከዚህ ቀደም ያልተመዘገበ ወሰንም። በማራቶን ብቻ ሳይሆን በሌሎች ስፖርቶችም ጭምር በ41 ዓመቱ ሜዳልያ ካጠለቀ፤ በእድሜ ትልቁ አሜሪካዊ ባለ ኦሊምፒክ ተሸላሚ ይሆናል። ይቅናህ መብ!
Received on Mon Apr 11 2016 - 13:15:52 EDT

Dehai Admin
© Copyright DEHAI-Eritrea OnLine, 1993-2013
All rights reserved