Ethsat.com/: እነ አቶ በቀለ ገርባ ጫማ ሳያደርጉ በሌሊት ልብስ ፍ/ቤት ቀረቡ

From: Berhane Habtemariam <Berhane.Habtemariam_at_gmx.de_at_dehai.org>
Date: Sat, 4 Jun 2016 01:22:50 +0200

እነ አቶ በቀለ ገርባ ጫማ ሳያደርጉ በሌሊት ልብስ ፍ/ቤት ቀረቡ

ኢሳት (ግንቦት 26 ፥ 2008)

June 3, 2016

ESAT Daily News Amsterdam June 03, 2016

http://video.ethsat.com/?p=24482

በኦሮሚያ ክልል የተቀጣጠለውን ህዝባዊ ተቃውሞ ተከትሎ በአሸባሪነት ተወንጅለው በቂሊንጦ ወህኒ ቤት የሚገኙት እነ አቶ በቀለ ገርባ ጫማ ሳያደርጉ በሌሊት ልብስ ፍ/ቤት ቀረቡ።

ቁምጣና ከነቴራ ለብሰው ባዶ እግራቸውን ችሎት ለመቅረብ የተገደዱት ልብሶቻቸው በወህኒ ቤቱ ሃላፊዎች ስልተወሰደባቸው እንደሆነም መረዳት ተችሏል።

አርብ ግንቦት 26 ፥ 2008 በሌሊት ልብስ እና በባዶ እግራቸው ችሎት የቀረቡት የኦሮሞ ፌዴራሊስት ኮንግሬስ ተቀዳሚ ም/ፕሬዝዳንት አቶ በቀለ ገርባ እንዲሁም ሌሎች የአመራር አባላት አቶ ደጀኔ ጣፋ፣ አቶ ጉርሜሳ አያና እንዲሁም አቶ አዲሱ ብላላን ጨምሮ በአጠቃላይ 22 ሰዎች መሆናቸውን ከተማሪዎች ቤተሰቦች ለመረዳት ተችሏል።

አርብ ግንቦት 26 ፥ 2008 ከፍተኛ ፍ/ቤት ባለባቸው ቀጠሮ ተቃውሞኣቸውን ለመግለጽ ጥቁር ልብስ ለብሰው ወደችሎቱ ለማምራት መወሰናቸውን ተከትሎ የእስር ቤቱ ሃላፊዎች ፍተሻ በማድረግ ልብሶቻቸውን በመውሰዳቸው በሌሊት ልብስ ችሎት የቀረቡት እነ አቶ በቀለ ገርባ፣ ከጥቁር ልብስ ባሻገር ሌሎች ልብሶቻቸውም መወሰዳቸው ተመልክቷል።

አቶ በቀለ ገርባ ከአምስት አመት በፊት በአሸባሪነት ተወንጅለው የተፈረድባቸውን እስራት አጠናቀው በወጡ በወራት ጊዜ ውስጥ ተመልሰው በአሸባሪነት ተወንጅለው መታሰራቸው ይታወቃል።

በህዳር ወር 2008 የተቀጣጠለውን የኦሮሚያ ክልል ተቃውሞ ተከትሎ በርካታ የኦሮሞ ፖለቲከኞች ምሁራንና አክቲቪስቶች መታሰራቸው ይታወቃል።

*********************************************************************************

በሃሮማያ ዩኒቨርስቲ የ288 ተማሪዎች መኖሪያ ዶርሚተሪ ተቃጠለ

June 3, 2016

ግንቦት ፳፮(ሃያ ስድስት) ቀን ፳፻፰ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-  መንስኤው በውል ባልታወቀ ሁኔታ በተነሳው ቃጠሎ ቀደም ብሎ ከመቃጠል የተረፉት ሁለቱ ብሎኮች በእሳት ጋይተዋል። ቀደም ብሎ በደረሰው ቃጠሎ የ587 ተማሪዎች መኖሪያ የሆኑ 5 ህንጻዎች ወድመው ነበር።

ለሳምንታት ትምህርት ያቋረጡት  የሃሮማያ ዩኒቨርስቲ ተማሪዎች፣ ትምህርታቸውን እንዲጀምሩ ካልጀመሩ ግን ከዩኒቨርስቲው እንደሚባረሩ ተነግሯቸዋል። የፌደራል ፖሊሶች ግቢውን ለቀው ለመውጣት የሚሞክሩ ተማሪዎችን ሰነዶች ሲቀሙ መታዬታቸውን ወኪላችን ገልጿል። በዩኒቨርስቲው የተጀመረው ተቃውሞ በኦሮምያ የተነሳው ተቃውሞ አካል ነው።

በሌላ በኩል በሃረር ከተማ የሚገኙ ወጣቶችና ሴቶች ከክልሉ ባለስልጣናት ጋር ዛሬ በማድረግ ላይ ባሉት ስብሰባ፣ ወጣቶቹ “በሃረሪ ክልል የሌሎች ክልሎች ተወላጆች ላይ የባርነት ስርዓት እየተተገበረ ነው፣ ሁለተኛ ዜጋ እድጋችሁናል፣ ወጣቱን ስራ አሳጥታችሁዋል፣ ፍትህ የለም፣ መልካም አስተዳደር የለም” በማለት ወጣቶቹ ጠንካራ አስተያየቶችን ሰጥተዋል።

ወጣቶቹ “ እናንተ የችግሩ አካል ሆናችሁ መፍትሄ ልትሰጡ አትችሉም፣ የምትጠሩት ስብሰባ በህዝብ ላይ ለመቀለድ እና እኛን ለመታዘብ እንዲሁም አልበቃችሁም ብላችሁ ሌላ ጭቆና ልታደርሱብን ነው” በማለት ተናግረዋል። በክልሉ ያለው የህዝብ ብሶት እየጨመረ መምጣቱን ስብሰባውን የተከታተለው ወኪላችን ገልጿል። ከሁለት ቀናት በፊት የክልሉ ፕሬዚዳንት ከነዋሪዎች ጋር ባደረጉት ስብሰባም ተመሳሳይ ጠንካራ ተቃውሞ ተነስቶ ነበር። ፕሬዚዳንቱ በሙስናና በመልካም አስተዳዳር የተዘፈቁ ጠበቆችን፣ ፖለሶችንና ሰራተኞችን ማባረራቸውን በመግለጽ የህዝቡን ቁጣ ለማብረድ ቢሞክሩም፣ ህዝቡ ግን የተጠራቀመ ብሶቱን ከመግልጽ አልተቆጠበም ነበር።

ከክልሉ ዜና ሳንወጣ ዛሬ ቀን 7 ሰአት ተኩል አካባቢ በሃረር አንደኛ መንገድ ላይ የቻይና የመንገድ ስራ ድርጅት ንብረት የሆነ ሬንጅ የሚረጭ ቦቴ መኪና ሙሉ በሙሉ ተቃጥሏል። የእሳት አደጋ መኪና ተጠርቶ ቢመጣም፣ መኪናው ምንም ውሃ ሳይዝ ቦታው ላይ ተገኝቷል። መኪናው ውሃ ለመቅዳት መመለሱን የገለጸው ወኪላችን፣ ህዝቡ በአፈርና በውሃ ተረባርቦ እሳቱን ማጥፋቱንና መኪናው ሙሉ በሙሉ መውደሙን ገልጿል። የቃጠሎው መንስኤ በትክክል አለመታወቁንም ገልጿል።  አሁን በደረሰን ዜና ደግሞ የ 1ኛ ዓመት የኢንጂነሪንግ ተማሪዎች ከዛሬ ጀምሮ ግቢውን ለቀው እንዲወጡ ተነግሮዋቸዋል ።

Received on Fri Jun 03 2016 - 19:22:51 EDT

Dehai Admin
© Copyright DEHAI-Eritrea OnLine, 1993-2013
All rights reserved