Goolgule.com: የአውሮጳ ኅብረት ድጎማ ህወሃት ኮሮጆ አይገባም። የኅብረቱ ውሳኔ ድንግዝግዝ ነው

From: Berhane Habtemariam <Berhane.Habtemariam59_at_gmx.de_at_dehai.org>
Date: Fri, 9 Sep 2016 23:57:49 +0200

የአውሮጳ ኅብረት ድጎማ ህወሃት ኮሮጆ አይገባም

የኅብረቱ ውሳኔ ድንግዝግዝ ነው
tplf-eu
 
 

ከሕገወጥ ፍልሰት ጋር በተያያዘ የአውሮጳ ኅብረት የአስቸኳይ ጊዜ መተማመኛ ድጎማ (Emergency Trust Fund – ETF) በማለት ለኢትዮጵያ የመደበው ገንዘብ ወደ ህወሃት ኮሮጆ እንደማይገባ ተነገረ፡፡ በኢትዮጵያ እየተባባሰ የመጣው የሰብዓዊ መብቶች ጥሰትን እንደምክንያት በማድረግ ድጎማው እንዲከለስ ወይም እንዲሰረዝ ዩሮአክቲቭ ያቀረበው ጥያቄ ለመረጃው ይፋ መሆን ምክንያት ሆኗል፡፡ አንድ ጊዜ በቃል በሌላ ጊዜ ደግሞ በኢሜይል ከኅብረቱ በኩል የተሰጠው መረጃ የኅብረቱን የድጎማ አከፋፈል በተመለከተ የጠራ አቋም የማያሳይ ድንግዝግዝ መረጃ ሆኗል፡፡

በህገወጥ መንገድ ከአፍሪካ የሚፈልሱት ዜጎች የአውሮጳውያን መንግሥታት ራስምታት ከሆኑ ዓመታት ተቆጥረዋል፡፡ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ የፍልሰት መጠኑ መጨመሩና ከዚያ ጋር ተያይዞ የሚጠፋው የሰው ህይወት አውሮጳውያኑን በስፋት ያነታረከ ነው፡፡ እንደ ማልታ፣ ጣሊያን ያሉ የመግቢያ አገሮች ከባህር የሚመጣውን የመቀበልና አደጋ ሲደርስ ፈጥኖ የመድረስ ግዴታቸው ለበርካታ የፋይናንስና የፖለቲካ ኪሣራ ዳርጓቸዋል፡፡ አውሮጳውያኑ ከአፍሪካ የሚፈልሱትን ለመቆጣጠር የተለያዩ ዘዴዎችን ቢጠቀሙም የታሰበውን ውጤት ግን አላመጡም፡፡ ከዚህ ሌላ በየጊዜው ከዚያው ከአውሮጳ አካባቢ አገራት (ሰርቢያ፣ ግሪክ፣ ሶሪያ፣ …) የሚፈልሱ ቁጥራቸው በርካታ ነው፡፡ ሁለቱን ዓይነት ፍልሰቶች ነጣጥሎ ለማከም ከአፍሪካ ለሚፈልሱት አውሮጳውኑ በማልታ የቫሌታ ከተማ ተሰብስበው የአስቸኳይ ጊዜ መተማመኛ ድጎማ (Emergency Trust Fund – ETF) አቋቋሙ፡፡2015_valletta_summit_on_migration-jpeg

በህዳር ወር 2008ዓም የተደረገውና የቫሌታ የፍልሰት ጉባዔ ተብሎ በተጠራው ስብሰባ ላይ የመፍትሔው ባለቤቶች የሆኑት አውሮጳውያን እና የችግሩ ፈጣሪዎች የአፍሪካ አምባገነኖች (ጥቂት ዴሞክራቶች መኖራቸው ሳይዘነጋ) ተገኝተዋል፡፡ የሱዳኑ አልበሽር ባህር የመሻገር ዕገዳ ስለተደረገባቸው በውጪ ጉዳያቸው ሲወከሉ የህወሃት ተወካይ ሃይለማሪያም ደሳለኝ በኢትዮጵያ ስም ተገኝተዋል፡፡ ሌሎች የአውሮጳ ኅብረት ድርጅቶችና የተባበሩት መንግሥታት መ/ቤቶችም ተሳታፊ ሆነዋል፡፡ ስብሰባው ከመጠናቀቁ በፊት ፍልሰትን ለመከላከል ሁለት አማራጮ ተወስደዋል፤ አንዱ የፍልሰቱ ምንጭ የሆኑ አገራት ዜጎችን በሚኖሩበት አገር የኢኮኖሚ ብቃት እንዲኖራቸው ማድረግ፤ ሁለተኛው ህጋዊ የስደትና የፍልሰት መንገዶችን ማመቻቸት፡፡ በጉባዔው ላይ ፍልሰትን ለመቆጣጠር የ1.8ቢሊዮን ዩሮ ለመስጠት ቃል የተገባ ሲሆን በአፍሪካ የሚረዱት አገራት በሦስት ተመድበው ኢትዮጵያ ያለችበት “የአፍሪካ ቀንድ” ምድብ ጂቡቲ፣ ኤርትራ፣ ኬኒያ፣ ሶማሊያ፣ ደቡብ ሱዳን፣ ሱዳን፣ ታንዛኒያና ዑጋንዳ እንዲካተቱ ተደርጓል፡፡፡

ድርብ አኻዝ የኢኮኖሚ ዕድገት እያመጣን ነው ለሚሉት የአፍሪካ አገራትም ሆነ ህወሃት በሚገዛት ኢትዮጵያ ለሚገኙ አምባገነኖች የሕዝብ ፍልሰትና ይህ ድጎማ እንደ ውርደት የሚቆጠር ቢሆንም እነርሱ ግን እጅ ነስተው ለመቀበል አንዳችም ኃፍረት አሳይተው አያውቁም፡፡ ድጎማው ሥራአጥነትን ለመቀነሰና ዜጎች የኢኮኖሚ አቅም እንዲኖራቸው በትምህርት፣ በሙያ፣ … ራሳቸውን በማነጽ ብቃትና ችግርን የመቋቋም ብርታት እንዲኖራቸው ታሳቢ ባደረጉ ሌሎች መርሃግብሮች ላይ ትኩረት ያደረገ ነው፡፡ ከዚህ ጋር በተያያዥነት በየአገራቱ የህግ የበላይነት እንዲኖርና መልካም አስተዳደር እንዲሰፍን፣ ሰብዓዊ መብቶች እንዲከበሩ በድጎማው ሥር የተካተቱት መርሃግብሮች ያስረዳሉ፡፡ ኢትዮጵያ ለምትገኝበት የአፍሪካ ቀንድ ቡድን እኤአ2020 ድረስ 714 ሚሊዮን ዩሮ በጀት ተይዟል፡፡ ይህ እንደ መነሻ የተበጀተ ሲሆን መጠኑ በየጊዜው እንደሚጨምር ይታመናል፡፡

ከዚህ የአስቸኳይ ጊዜ መተማመኛ ገንዘብ ሌላ የትግራይ ሕዝብ ነጻአውጪ ግምባር (ህወሃት) ለሚገዛት ኢትዮጵያ የአውሮጳ ኅብረት በርካታ ድጎማ ያደርጋል፡፡ ህወሃት ዕድገትና ትራንስፎርሜሽን በተባለው የመለመኛ ስልት ባቀረበው መረጃ መሠረት የአውሮጳ ኅብረት ከ2014-2020 (እኤአ) ላሉት ዓመታት ለእርሻና ለምግብ ዋስትና 252.4 ሚሊዮን ዩሮ፤ ለጤና 200 ሚሊዮን ዩሮ፤ ለመንገድ ሥራና ኃይል አቅርቦት 230 ሚሊዮን ዩሮ፣ ለሲቪል ማኅበረሰብና አስተዳደር 52 ሚሊዮን ዩሮ፤ ለሌሎች የድጋፍ ተግባራት 10.6 ሚሊዮን ዩሮ በድምሩ 745 ሚሊዮን ዩሮ ወይም በትንሹ የ20 ቢሊዮን ብር እርዳታ ፈቅዷል፡፡ ይህ ማለት በመካከል በድንገት የሚፈጠሩ ዕርዳታዎችን ሳይጨምር ነው፡፡ (በአየር መዛባት ምክንያት የአስቸኳይ ዕርዳታ ለሚያስፈልጋቸው በሚል በዚህ ዓመት የሚያዚያ ወር ኅብረቱ 122.5 ሚሊዮን ዩሮ ዕርዳታ ሰጥቷል፡፡ ይህ ደግሞ በታህሳስ ወር ለኤልኒኞ አስቸኳይ ዕርዳታ በሚል 79 ሚሊዮን ዩሮ ለአፍሪካ ቀንድ ሲመደብ 43 ሚሊዮን ለኢትዮጵያ ከተሰጠው በተጨማሪ ነው)፡፡ እስካሁን ከተሰጡት ዕርዳታዎች ሌላ እኤአ 2009-2013 ባሉት ዓመታት ኅብረቱ 674 ሚሊዮን ዩሮ መስጠቱ ይታወቃል፡፡ በጥቅሉ ከ2009-2020 ባሉት ዓመታት ኅብረቱ በትንሹ 1.6ቢሊዮን ዩሮ ወይም ከ40ቢሊዮን ብር የሚበልጥ ድጎማ ሰጥቷል/ይሰጣል፡፡

etfየአውሮጳ ኅብረት ሕገወጥ ፍልሰትን ለመከላከል የመደበውና ህወሃት ወደ ኮሮጆው ሊያስገባው የተመኘው ዕርዳታ ግልጽ ባለ መልኩ ባይረጋገጥም ትልቅ ዕንቅፋት ገጥሞታል፡፡ በተያዘው ዕቅድ መሠረት የአስቸኳይ ጊዜ ዕርዳታው (ETF) እኤአ እስከ 2020 ላሉትዓመታት 714 ሚሊዮን ዩሮ ኢትዮጵያ ለምትገኝበት የአፍሪካ ቀንድ ቡድን መድቧል፡፡ የአውሮጳውያኑ 2016ዓም ከመጀመሩ በፊት የህገወጥ ፍልሰትን መነሻ ምክንያቶችን በቅድሚያ ለመከላከል በሚል ኅብረቱ 253 ሚሊዮን ዩሮ መድቦ ነበር፡፡ ለደቡብ ሱዳን ከተመደበው በ10 ሚሊዮን ዩሮ በማነስ የፍልሰት መነሻ አካባቢዎች የሥራ ዕድል ለመፍጠር በሚል 67 ሚሊዮን ዩሮ በ2016ዓም ለኢትዮጵያ እንዲደርስ ተደርጓል፡፡ ከዚህ ሌላ አገር ያልተሰየመለት ነገር ግን ሕገወጥ የሰው ዝውውር ለመዋጋት 40 ሚሊዮን ዩሮ ተመድቧል፡፡ ከ67 ሚሊዮኑ ውስጥ 20 ሚሊዮኑ ሕገወጥ ፍልሰትን ከመነሻው ለመከላከል ለትግራይ፤ ለአማራ፤ ለኦሮሚያና ለደቡብ ህዝብ ሲመደብ የተቀረው 47 ሚሊዮን ደግሞ በአፋር፣ በአማራ፣ በኦሮሚያ፣ በደቡብ ህዝብና በሶማሊ ክልሎችና በተለይ ለድርቅ ተጋላጭ አካባቢዎች የሚኖሩ ዜጎች በኢኮኖሚ እንዲያድጉ፣ ሥራ በመፍጠር ኑሯቸውን እንዲያሻሽሉ፣ መሠረታዊ የውሃ፣ የጤና፣ የንጽህና አጠባበቅ አገልግሎት በማግኘት ራሳቸውን በማጎልበት ፍልሰትን እንዲከላከሉ ተመድቧል፡፡

ከላይ እንደተጠቀሰው 67 ሚሊዮኑ ለዚህ ዓመት (2016) ከተመደበ ዘጠኝ ወራት ተቆጥረዋል፡፡ የገንዘቡ ፍሰት በምን ዓይነት መልኩ እንደሚከናወን ወይም እስካሁን እንዴት እንደተከናወነ የተሰጠ መረጃ የለም፡፡ የድርብ አኻዝ ዕድገት አስቆጥሬአለሁ የሚለው ህወሃት/ኢህአዴግ በኢትዮጵያ ሕዝብ ላይ እየፈጸመ ያለው የሰብዓዊ መብት ገፈፋ ያሳሰበው በአውሮጳ ኅብረት ጉዳዮች ላይ በመዘገብ ዕውቅና ያተረፈው EurActiv Network የተባለ የድረገጽ ሚዲያ የገንዘቡን አፈሳሰስ በተመለከተ ለሚመለከተው የኅብረቱ አካል ጠንከር ያለ ጥያቄ አቅርቦ ነበር፡፡

የኅብረቱ ወዳጅ ለሆነው የህወሃት አገዛዝ በሕዝቡ ላይ የሚፈጽመው አሰቃቂ በደል በይፋ እየታየ ባለበት ባሁኑ ወቅት ኅብረቱ ይህንን የፍልሰት መከላከያ ዕርዳታ አሰጣጥ እንደገና ለመከለስ ወይም ለማቆም ያቀደው ነገር እንዳለ EurActiv ይጠይቃል፡፡ በአዲስ አበባ ለሚገኘው አገዛዝም ሆነ በሥሩ ላሉት መ/ቤቶች ገንዘቡ በቀጥታ እንዳልተላከ የአውሮጳ ኅብረት አፈቀላጤ ምላሽ ሰጥተዋል፡፡ በቀጣይ አፈቀላጤው በኢሜይል ለ EurActiv በላኩት መልዕክት የአስቸኳይ ጊዜ ድጎማው (ETF) በአፍሪካ ለሚገኙ መንግሥታትም ሆነ መዋቅሮቻቸው ሥር ለሚገኙ መ/ቤቶች በቀጥታ የማይሰጥ መሆኑና በዚህ አሠራር ውስጥ ኢትዮጵያ የምትካተት መሆኗን አስረድተዋል፡፡ ምናልባት የዚህ ዓመቱ (2016) ድጎማ በባለራዕዩ መሪ አባባል “እስከ እንጥሉ ለገማው” ህወሃት/ኢህአዴግ በቀጥታ ለመሄዱ እርግጠኛ ለመሆን ባይቻልም ከዚህ በኋላ የሚላከው ወደ ህወሃት ኮሮጆ እንዳይገባ ዩሮአክቲቭ ያቀረበው አቤቱታ ደንቃራ ሆኗል፡፡

ከዚህ ጋር በተያያዘ የEurActiv የዜና ዘገባ እንዳመለከተው የአውሮፓ ኅብረት በኢትዮጵያ ያለውን የሰብዓዊ መብት ሁኔታ እየተከታተለ እንደሆነና በከፍተኛ የፖለቲካ አመራር ደረጃ በኢትዮጵያ ካለው (አገዛዝ) ጋር ላይ እየተገናኘ እንደሆነ አፈቀላጤው አስረድተዋል፡፡

ህወሃት አብቅቶለታል” ከምትለው አሜሪካ ጀምሮ በይፋ ባይነገርም አውሮጳውያኑም በህወሃት ላይ አቋም መያዝ ከጀመሩ ሰነባብተዋል፡፡ ምዕራባውያን የዜና ዘገባዎችም ኢትዮጵያ በአናሳ የትግራይ ተወላጆች ቁጥጥር ሥር መውደቋን እና የአገሪቱ ኢኮኖሚ፣ መከላከያ፣ ደኅንነት፣ … በሙሉ 6በመቶ በሚሆኑ ትግራዮች መያዙን በተደጋጋሚ እየዘገቡ ነው፡፡ የምዕራቡን ዓለም ፖለቲካ በመዘወር ትልቅ ሚና የሚጫወቱ የሚዲያ ተቋማት በህወሃት ላይ ዘመቻ የያዙ በሚመስል መልኩ ዝምታቸውን ሰብረዋል፡፡ ከመጋረጃው በስተጀርባ የሚደረጉ ንግግሮች እንደሚያመለክቱት ህወሃት የአሜሪካ እና የአውሮጳውያን ታዛዥ ሆኖ ለመቆየት የሚያደርገው ስልቶች ሁሉ ያለቁበት ይመስላል፡፡ የሁልጊዜ ወዳጅ የሌላቸው ምዕራባውያንም የሕዝብ ተቃውሞ በርትቶ የህወሃት የፖለቲካ ድራማ የሚጠናቀቅበት ደረጃ ሲደርስ አቋማቸውን ከሕዝብ ጋር ለማድረግ ጊዜ እንደማወስድባቸው በግብጹ ሙባረክ ላይ ደረጉት የቅርብ ጊዜ ትዝታ ነው፡፡

 
Received on Fri Sep 09 2016 - 16:36:54 EDT

Dehai Admin
© Copyright DEHAI-Eritrea OnLine, 1993-2013
All rights reserved