Ethsat.com: በቂሊንጦ የጸጥታ ሃይሎች በእስረኞች ላይ የጅምላ የተኩስ እርምጃን ሲወስዱ እንደነበር ተገለጸ

From: Berhane Habtemariam <Berhane.Habtemariam59_at_gmx.de_at_dehai.org>
Date: Wed, 7 Sep 2016 00:00:17 +0200
በቂሊንጦ የጸጥታ ሃይሎች በእስረኞች ላይ የጅምላ የተኩስ እርምጃን ሲወስዱ እንደነበር ተገለጸ

ኢሳት (ጳጉሜ 1 ፥ 2008)

September 6, 2016

Watch these News:

ESAT DC Daily News Mon 05 Sep 2016

http://video.ethsat.com/?p=27958

ESAT Latest News Amsterdam September 06, 2016

http://video.ethsat.com/?p=27967

ESAT Daily News Amsterdam September 06, 2016

በሳምንቱ መገባደጃ ቅዳሜ በቂሊንጦ እስር ቤት የደረሰውን የእሳት አደጋ ተከትሎ የእስር ቤቱ የጸጥታ ሃይሎች በእስረኞች ላይ የጅምላ የተኩስ እርምጃን ሲወስዱ እንደነበር በእለቱ በእስር ቤቱ ጥበቃ ስራ ላይ ተሰማርቶ የነበረ የጸጥታ ባልደርባ ገለጸ።

ለደህንነቱ ሲል ስሙን ያልገለጸው ይኸው የቂሊንጦ እስር ቤት ጠባቂ በ20 ደቂቃ አምስት እስረኞች በኢላማ ተኩስ ተገድለው መመልከቱን አዲስ አበባ ውስጥ ለሚታተመው አዲስ ስታንዳርድ ጋዜጣ አስረድቷል።

መሳሪያን ሳይታጠቅ በእለቱ በጥበቃ ስራ ላይ ተሰማርቶ እንደነበር የገለጸው የቂሊንጦ እስር ቤቱ የጸጥታ ባልደርባ እሱን ጨምሮ ሌሎች ያልታጠቁ የጸጥታ አባላት በእለቱ እስረኞች ሊጠይቁ የመጡ ሰዎችን እንዲመለሱ ትዕዛዝ ተላልፎ እንደነበር ይፋ አድርጓል።

በእስር ቤቱ የደረሰውን የእሳት ቃጠሎ ለማጥፋት እስረኞች ጥረት ሲያደርጉ እንደነበር ያወሳው የጸጥታ ባልደልባ ከቅዳሜ ጀምሮ እሱና ሌሎች ባልደርቦች ወደ ቂሊንጦ እስር ቤት እንዳይገቡ መደረጉን አክሎ አስረድቷል።

በአዲስ አበባ ማረሚያ ቤት አስተዳደር ስር ይተዳደር የነበረው የቂሊንጦ እስር ቤት፣ በአሁኑ ወቅት በፌዴራል የጸጥታ ሃይሎች ቁጥጥር ስር እንዲሆን መደረጉን አደጋው በደረሰ ወቅት በስራ ላይ የነበረው የጸጥታ ባልደርባ አመልክቷል።

በተኩስ እርምጃ የተገደሉ 18 እስረኞችን ከእስር ቤት ለማውጣት ተሳትፎ እንደነበረው የገለጸው እማኝ አንድ እስረኛ ብቻ በእሳት ቃጠሎ መሞቱን ገልጿል።

መንግስት በቂሊንጦ እስር ቤት ደርሶ በነበረው የእሳት አደጋ 21 እስረኞች በእሳት ጢስ በመታፈንና በመረጋገጥ መሞታቸውን መግለጹ ይታወሳል።

ይሁንና በዕለቱ በጥበቃ ስራ ላይ ተሰማርቶ የነበረው ባልደርባ አንድ እስረኛ ብቻ በእሳት አደጋ መሞቱን አረጋግጦ የታጠቁ የቂሊንጦ የጸጥታ ሃይሎች የጅምላ የተኩስ እርምጃ መውሰዳቸውን ለህዝብ ይፋ እንዲሆን በፈለገው እማኝነት ለመጽሄቱ አስረድቷል።

የቂሊንጦው እስር ቤት እስከ ማክሰኞች ድረስ ከባድ መሳሪያን በታጠቁ የፌዴራል የጸጥታ ሃይሎች ጥበቃ እየተደረገለት እንደሚገኝና ማንም ሰው ወደ ስፍራው እንዳይጠጋ እገዳ መጣሉን ለመረዳት ተችሏል።

በእስር ቤቱ የነበሩ የፖለቲካ እስረኞች፣ የሰብዓዊ  መብት ተሟጋች ግለሰቦች፣ ጋዜጠኞች እንዲሁም የሃይማኖት መሪዎች የደህንነታቸው ሁኔታ ሊረጋገጥ አለመቻሉ ታውቋል።

********************************************************************************

ቁጥራቸው የማይታወቅ እስረኞች በሆስፒታሎች ህክምና እየተደረገላቸው ነው

ኢሳት (ጳጉሜ 1 ፥ 2008)

September 6, 2016

ሰሞኑን በቂሊንጦ እስር ቤት የደረሰውን የእሳት አደጋ ተከትሎ የገቡበት ካልታወቀው ወደ ሶስት ሺ አካባቢ እስረኞች መካከል በርካቶች በተለያዩ የአዲስ አበባ ሆስፒታሎች ህክምና እየተደረገላቸው መሆኑ ተገለጸ።

የቂሊንጦ ማረሚያ ቤት አስተዳደር በበኩሉ ለ8 ሰዓታት ያህል የቆየው የእሳት አደጋ የእስረኞቹን ንብረቶችና መጠለያ ቤቶች ሙሉ ለሙሉ ማውደሙን ማክሰኞ ለሃገር ውስጥ መገናኛ ብዙሃን በሰጠው መግለጫ አመልክቷል።

ደርሷል የተባለው የእሳት አደጋ ለስምንት ሰዓታት ያህል መቆየቱ ቢገልፅም፣ በቅርብ ርቀት ላይ የሚገኙ የአዲስ አበባ ከተማ እሳት ማጥፊያ ተሽከርካሪዎች በምን ምክንያት እሳቱን ለረጅም ሰዓታት መቆጣጠር እንዳልቻለ የተገለፀ ነገር የለም።

በእስር ቤት ለሰዓታት የቆየ የተኩስ ድምፅ እንደነበር የሚናገሩት እማኞች በበኩላቸው፣ በርካታ ጉዳት የደረሰባቸው እስረኞች ወዳልታወቀ ቦታ ሲጓጓዙ ማየታቸውን አስረድተዋል።

አዲስ አበባ ከተማ በሚገኙ የመንግስት ሆስፒታሎች እነዚሁ እስረኞች ጥበቃ እየተደረገላቸው ህክምና እያገኙ እንደሆነ ከሃገር ቤት ከተገኘ መረጃ ለመረዳት ተችሏል።

መንግስት በአደጋው 23 እስረኞች መሞታቸው ይፋ ቢያደርግም የሟቾችን ማንነት ግን ከመግለጽ ተቆጥቦ ይገኛል። የእስረኛ ቤተሰቦች በበኩላቸው ማክሰኞ ድረስ የቤተሰብ አባሎቻቸውን ሁኔታ ለማወቅ ያደረጉት ጥረት አለመሳካቱን አስታውቀዋል።

የቂሊንጦ ማረሚያ ቤት አስተዳደር እስር ቤቱ ሙሉ ለሙሉ በእሳት አደጋው በመውደሙ ምክንያት እስረኞቹ ወደተለያዩ የፌዴራል እስር ቤቶች መዛወራቸውን ማክሰኞች ቢገልፅም፣ እስረኞቹ የሚገኙበትን ስፍራ ከመግለጽ ተቆጥቧል።

የቤተሰብ አባሎቻቸው የገቡበትን ለማወቅ ተቸግረው የሚገኙ ሰዎች በበኩላቸው፣ መንግስት የሟቾችን ማንነት ይፋ እንዲያደርግና የተቀሩትም ያሉበትን ስፍራ ለጉብኝት ክፍት እንዲያደርግ ጠይቀዋል።

የእስረኛ ቤተሰቦች ማክሰኞ በጥቁር አንበሳ፣ ፓውሎስ ሆስፒታልና ሌሎች ሆስፒታሎች በመገኘት የቤተሰብ አባሎቻቸውን ሁኔታ ለማወቅ ያደረጉት ጥረት አለመሳካቱን ከሃገር ቤት የደረሰን መረጃ አመልክቷል።

የፓርቲ አመራሮችን ጨምሮ የተለያዩ አለም አቀፍ የሰብዓዊ መብት ተሟጋች ድርጅቶች በቂሊንጦ እስር ቤት የደረሰውን የእሳት አደጋ ተከትሎ መንግስት መረጃዎችን ይፋ እንዲያደርግ እየጠየቁ ይገኛል።

********************************************************************************

በነቀምቴ ከተማ ሁለት የአጋዚ ወታደሮች ሲገደሉ ሌላ አንድ መቁሰሉ ተነገረ

ኢሳት (ጳጉሜ 1 ፥ 2008)

September 6, 2016

በምዕራብ ኦሮሚያ ክልል ስር በምትገኘው የነቀምቴ ከተማ ማክሰኞ ምሽት ማንነታቸው ያልታወቁ አካላት በመከላከያ ሰራዊት አባላት ላይ በፈጸሙት የቦንብ ጥቃት ሁለት የአጋዚ ወታደሮች መገደላቸውንና ሌላ አንድ ወታደር መጎዳቱን እማኞች ለኢሳት ገለጹ። ወተደሮቹ ትቃቱ የተፈጸመባቸው በአካባቢው ነዋሪዎች ላይ ወከባ ማድረሳቸው አስመርሯቸው እንደሆነ ተመልክቷል።

ወታደሮቹ ላይ የተፈጸመው ጥቃት በከተማዋ ቀበሌ 07 ውስጥ በሚገኝ አንድ የመንግስት ድርጅት ውስጥ መከሰቱን ለደህንነታቸው ሲሉ ስማቸውን መግለጽ ያልፈለጉ የከተማዋ ነዋሪዎች ከዜና ክፍላችን ጋር ባደረጉት ቃለምልልስ አስረድተዋል።

በመከላከያ ሰራዊት አባላቱ ላይ የተፈጸመውን የቦንብ ጥቃት ተከትሎ የአጋዚ ወታደሮች በወሰዱት የአጸፋ እርምጃ፣ ከጥቃቱ ጋር ግንኙነት የሌላቸው ሶስት የወለጋ ዩኒቨርስቲ ተማሪዎች መገደላቸውን የሟቾችን ስም በመግለጽ እማኞች ለኢሳት አስታውቀዋል።

በከተማ የስራ ማቆም አድማ በመካሄድ ላይ መሆኑን የተናገሩት የነቀምቴ ከተማ ነዋሪዎች፣ ግድያ የተፈጸመባቸው ሶስቱ የዩኒቨርስቲ ተማሪዎች በወለጋ የሆሮ ጉድሩ አካባቢ ነዋሪዎች ሲሆን፣ አስሬናቸው ወደ መኖሪያ ቀያቸው መሸነኘቱን ነዋሪዎች ገልጸዋል።

በኦሮሚያ ክልል ለወራት በመካሄድ ላይ ያለውን ህዝባዊ ተቃውሞ ለመቆጣጠር በሺዎች የሚቆጠሩ የፌዴራል መከላከያ ሰራዊትና የአጋዚ ልዩ ሃይሎች በወለጋና የተለያዩ የክልሉ ቦታዎች ሰፍረው እንደሚገኙ ይታወቃል።

በክልሉ ተቃውሞን እያሰሙ የሚገኙ ነዋሪዎች እነዚሁ ሃይሎች አካባቢውን ለቀው እንዲወጡና ግድያ እንዲቆም በመጠየቅ ላይ መሆናቸውን ከሃገር ቤት የተገኘ መረጃ አመልክቷል።

ሂውማን ራይትስ ዎችን ጨምሮ የተለያዩ አለም አቀፍ የሰብዓዊ መብት ተሟጋች ድርጅቶች በኦሮሚያ ክልል ለወራት ከተቀጣጠለው ተቃውሞ ጋር በተገኛኘ እስካሁን ድርስ ወደ 500 አካባቢ ሰዎች መሞታቸውን በመግለጽ ላይ ናቸው።

ይሁንና መንግስት በርካታ ሰዎች ለእስር መዳረጋቸውን ቢገልጽም፣ በጸጥታ ሃይሎች የተገደሉ ስዎችን ቁጥር ግን ከመግለጽ ተቆጥቧል።

********************************************************************************

በኦሮሚያ የስራ ማቆም አድማ ተጀመረ

ኢሳት (ጳጉሜ 1 ፥ 2008)

September 6, 2016

ከአዲስ አበባ ከተማ በቅርብ ርቀት ላይ በምትገኘው የአምቦ ከተማን ጨምሮ በተለያዩ የኦሮሚያ የክልል ከተሞች ማክሰኞ የስራ ማቆም አድማ መጀመሩን ነዋሪዎች ለኢሳት አስታወቁ።

በአምቦና ጉደር አካባቢ የንግድ ተቋማትን ጨምሮ የተለያዩ አገልግሎቶች መስጫ ተቋማት የስራ ማቆም አድማ በማድረግ ላይ መሆናቸውን በጉዳዩ ዙሪያ ከኢሳት ጋር ቃለምልልስን ያደረጉ ነዋሪዎች አስረድተዋል።

መንግስት በክልሉ እንዲሁም በተለያዩ የሃገሪቱ አካባቢዎች እየወሰደ ያለውን ግድያና አፈና በመቃወም የስራ ማቆም አድማው መጀመሩን እማኞች የገለጹ ሲሆን፣ የመንግስት አካላት አድማው እንዳይካሄድ ያደረጉት ዘመቻ አለመሳካቱን ከነዋሪዎቹ ለመረዳት ተችሏል።

የአምቦ ከተማ አስተዳደር ማክሰኞ የስራ ማቆም አድማው ላይ በሚሳተፍ የንግድ ተቋማት ላይ እስከ አምስት ሺ ብር የሚደርስ ቅጣትን ለመጣል ማሳሰቢያን ቢሰጥም፣ ሁሉም ድርጅቶች ማክሰኞ በአድማው ተሳታፊ መሆናቸውን ነዋሪዎች ገልጸዋል።

ነዋሪዎች የወሰዱትን ዕርምጃ ተከትሎ የየከተሞቹ የንግድ ቢሮዎች የንግድ ተቋማት ላይ “ታሽጓል” የሚል ወረቀት እየለጠፉ ሲሆን፣ ከአምቦ ወደ ጉደር ከተማ ለመንግስት ስራ በየዕለቱ የሚንቀሳቀሱ ሰዎች ማክሰኞ የስራ እንቅስቃሴያቸው መስተጓጎሉን ከኢሳት ጋር ቃለምልልስን ያደረጉ እማኞች አስረድተዋል።

በተመሳሳይ ሁኔታም በነቀምቴ ከተማና አካባቢው ተመሳሳይ የስራ ማቆም አድማ ማክሰኞ መጀመሩን የአካባቢው ነዋሪዎች ከዜና ክፍላችን ጋር ባደረጉት ቃለምልልስ ገልጸዋል።

በአምቦና ጉደር ከተሞች ያለውን የስራ ማቆም አድማ መንግስት ሊቆጣጠረው አልቻለም ሲሉ የተናገሩት ነዋሪዎች ህዝቡ ሰላማዊ ተቃውሞን አጠናክሮ ለመቀጠል እና የተለያዩ ስልቶችን ለመጠቀም እራሱን እያስተባበረ እንደሚገኝ አክለው አስታውቀዋል።

በተያያዘ ሁኔታም አዲስ አበባ ከተማን ጨምሮ በዙሪያዋ ባሉ የኦሮሚያ ክልል ከተሞች የአዲስ አመት የበዓል ዝግጅት ከተለመደው ጊዜ የቀዘቀዘ መሆኑን ነዋሪዎች ይገልጻሉ።

Received on Tue Sep 06 2016 - 16:39:22 EDT

Dehai Admin
© Copyright DEHAI-Eritrea OnLine, 1993-2013
All rights reserved