Ethsat.com: በቂሊንጦ እስርቤት የነበሩ ወደሶስት ሺ የሚጠጉ እስረኞች እስካሁን የደረሱበት አልታወቀም

From: Berhane Habtemariam <Berhane.Habtemariam59_at_gmx.de_at_dehai.org>
Date: Tue, 6 Sep 2016 00:42:26 +0200

በቂሊንጦ እስር ቤት እሳት ከመነሳቱ በፊት እስረኞች በጥይት መገደላቸውን ተገለጸ

September 5, 2016

ኢሳት (ነሃሴ 30 ፥ 2008)

Watch these:

http://video.ethsat.com/?p=27948

http://video.ethsat.com/?p=27936

በቂሊንጦ እስር ቤት እሳት ከመነሳቱ በፊት እስረኞች መገደላቸውንና የእሳት ቃጠሎ የተፈጸመው ግድያውን ለመሸፈን ሆን ተብሎ የተደረገ እንደሆነ የኢሳት ምንጮች ገለጹ።

ቅዳሜ ዕለት ንጋት ላይ ከ2:30 ጀምሮ ለሁለት ሰዓታት ያህል እስር ቤቱ በእሳት የጋየ ሲሆን፣ ከእሳቱ ሸሽተው ህይወታቸውን ለማዳን የሞከሩ ሰዎች ማማ ላይ በነበሩ ጠባቂዎች በተተኮሰ ጥይት ግድያ ተፈጽሞባቸዋል።

የኢሳት ምንጮች እንደገለጹት ከእስር ቤት ሊያመልጡ ሲሉ ሆን ተብሎ በተቀነባበረ ሴራ 4 እስረኞች ከተገደሉ በኋላ እስር ቤቱ በእሳት እንዲያያዝ ተደርጓል። ከዚያ ከቀጠሎ ለመሸሽ የሞከሩትን ማማ ላይ ሆነው ጥበቃ ላይ በነበሩ ፖሊሶች ጥይት ተርከፍክፎባቸዋል።

ከአሰቃቂው ጭፍጨፋ በኋላ እስር ቤቱ የተዘጋ ሲሆን፣ ከ60 የሚበልጡ ግድያ የተፈጸመባቸው እስረኞች አስከሬን በተለያዩ ሆስፒታሎች ከቤተሰብ ተደብቀው ተቀምጠዋል።

አስከሬኖቹ በጦር ሃይሎችና በአብዮት ሆስፒታል እንደሚገኙ ሲነገር፣ በሆስፒታል ውስጥ ባለው አስከሬን ማቆያ ማንነታቸው እንዳይታወቅ በኮድ መቀመጣቸውን የኢሳት የሆስፒታል ምንጮች ጠቁመዋል። ከእነዚህ አስከሬኖች ውስጥ በአብዮት ሆስፒታል የነበሩ በወታደር መኪና ወደ ሌላ ቦታ መወሰዳቸውን አስረድተዋል።

ሃኪሞች አንድም ሰው በእሳት ተቃጥሎ እንዳልሞተ ያረጋገጡ ሲሆ፣ በሆስፒታሎች የሚገኙት አስከሬኖች በጥይት የተበሳሱ እንደሆነም ገልጸዋል። እስካሁን ድረስ በአብዮት ሆስፒታል ከ26 በላይ አስከሬኖች ተቆልፎባቸው ከቤተሰቦቻቸው ተደብቀው ይገኛሉ።

ከ3 ሺ በላይ እስረኞች ቤተሰቦች “ቂሊንጦ ተዘግቷል ሌላ ቦታ ፈልጉ” በመባላቸው በማዕከላዊ፣ በዝዋይ፣ በሸዋሮቢት፣ በቃሊቲ እና ሌሎች እስር ቤቶች ፍለጋ ቢያደርጉም ጥሩ ዜና መስማት አልቻሉ። የኦፌኮ አመራር ደጀኔ ጣፋ ባለቤት ወይዘሮ አሰለፈች ሙላቱ የ3 ቀን ጥረታቸው ተስፋቸውን እንዳጨለመና በየሆስፒታሉ ያለው ጥበቃ ስጋታቸውን እንደጨመረ ገልጸዋል።

የቂሊንጦ እስር ቤት አስተዳደር እሁድ ዕለት በ3 ቀናት ውስጥ አሳውቃለሁ ቢልም ዛሬ ከ5 ቀናት በኋላ ዝርዝራቸው እንደሚያሳውቅ ገልጿል።

********************************************************************************

በቂሊንጦ እስርቤት የነበሩ ወደሶስት ሺ የሚጠጉ እስረኞች እስካሁን የደረሱበት አልታወቀም

September 5, 2016

ኢሳት (ነሃሴ 30 ፥ 2008)

በሳምንቱ መገባደጃ ቅዳሜ በቂሊንጦ እስር ቤት የደረሰን የእሳት አደጋ ተከትሎ ወደ ሶስት ሺ የሚጠጉ እስረኞች ለሶስተኛ ቀን የገቡበት አለመታወቁ አሳስቦት እንደሚገኝ የኦሮሞ ፌዴራሊስት ኮንግሬስ (ኦፌኮ) ሰኞ አስታወቀ።

የእስረኞቹ ወደ ዝዋይና ሸዋ ሮቢት ተዛውረዋል ተብሎ ቢገለፅም፣ የታሳሪ ቤተሰቦት ወደ ስፍራው ሄደው እስረኞቹ እንደሌሉ ተነግሯቸው መመለሳቸውንና ድርጊቱ እጅግ አሳሳቢ መሆኑን የኦፌኮ ምክትል ሊቀመንበር አቶ ሙላቱ ተሾመ ከዜና ክፍላችን ጋር ባደረጉት ቃለ-ምልልስ አስረድተዋል።

መንግስት እስረኞቹ ያሉበትን ሁኔታ እንዲሁም በእሳት ቃጠሎው ወቅት ሲካሄድ የነበረን የተኩስ እርምጃ ተከትሎ የሞቱ እሰረኞችን ቁጥር እስካሁን ድረስ ግልፅ አለማድረጉ ከህግ አንጻር ተገቢ አለመሆኑን ደግሞ የህግ አካላት በመግለጽ ላይ ናቸው።

በቂሊንጦ እስር ቤት የደረሰውን አደጋ ምክንያት በማድረግ ከኢሳት ጋር ቃለ-ምልልስን ያደረጉት የኦፌኮ ምክትል ሊቀመንበር አቶ ሙላቶ ተሾመ የታሳሪ ቤተሰቦች የቤተሰቦቻቸውን ሁኔታ ለማወቅ እያደረጉ ያለው ጥረት ውጤት አለማገኘቱን ገልጸዋል።

ከአዲስ አበባ ከተማ በቅርብ ርቀት ላይ ወደ ሚገኘው የቂሊንጦ እስር ቤት በርካታ ሰዎች የታሳሪ ቤተሰቦቻቸውን ሁኔታ ለማወቅ ቢጓዙም የመንግስት የጸጥታ ሃይሎች ህዝቡን ከሶስት ኪሎሜትር ርቀት ላይ እንዳያልፉ ማድረጋቸው ታውቋል።

በርካታ አባላቱ በዚሁ እስር ቤት ይገኙበት የነበረው የኦሮሞ ፌዴራሊስት ኮንግሬስ በእስር ቤቱ ወደ ሶስት ሺ የሚጠጉ የፖለቲካ፣ የሃይማኖትና ሌሎች እስረኞች ይገኙ እንደነበር ገልጿል።

ይሁንና የሁሉም እስረኞች ሁኔታ ለሶስተኛ ቀን ሰኞ ምሽት ድረስ ምንም ሊታወቅ አለመቻሉን ያስታወቀው ፓርቲው፣ በአባላቱና በእስረኞቹ ደህንነት እጅግ አሳስቦት እንደሚገኝ አክሎ አመልክቷል።

በህገ-መንግስቱ የተቀመጡ የእስረኞች መብት አለመከበሩን የተናገሩት የፓርቲው አመራር አቶ ሙላቱ ተሾመ መንግስት ያለበትን ሃላፊነት እንዲወጣ በፓርቲውና በታሳሪ ቤተሰቦች ስም ጥሪን አቅርበዋል።

በቂሊንጦ እስር ቤት ቅዳሜ የተሰማን የተኩስ ድምፅ ተከትሎ በትንሹ 20 ሰዎች መገደላቸውን በሃገር ውስጥ ያሉ መገኛኛ ብዙሃን የዘገቡ ሲሆን፣ የተለያዩ አካላት የሟቾች ቁጥር ሊጨምር እንደሚችል ስጋታቸውን በመግለጽ ላይ ናቸው።

የህግ ባለሙያዎቹ በበኩላቸው መንግስት በእስር ቤቱ የተፈጠረውን ድርጊት በአግባቡ ለህዝቡ አለማሳወቁ ከህግም ሆነ ከሰብዓዊነት አንጻር ተገቢ አለመሆኑን ከኢሳት ጋር ባደረጉት ቃለምልልስ አስረድተዋል።

ይህ በእንዲህ እንዳለ ቅዳሜ በቂሊንጦ እስር ቤት የደረሰን የእስት አደጋ ተከትሎ ቁጥራቸው ሊታወቅ ያልቻለ እስረኞች መሞታቸውን BBC ሰኞ ዘግቧል።

በዚሁ እስር ቤት ደርሷል የተባለውን የእሳት ቃጠሎ ተከትሎ በእስር ቤቱ የተኩስ ድምፅ ሲሰማ መቆየቱን የዜና አውታሩ የተለያዩ አካላትን ዋቢ በማድረግ ያቀረበ ሲሆን፣ በሃገሪቱ ለወራት የዘለቀ ተቃውሞ በመካሄድ ላይ መሆኑን አክሎ አመልክቷል።

የብሪታኒያው የማሰራጫ ጣቢያ ቢቢሲ የኢሳትን የቴለቪዥን ዘገባ ዋቢ በማድረግ በቂሊንጦ እስር ቤት የነበረን የእሳት አደታ ቃጠሎ በሪፖርቱ አስደግፎ አቅርቧል።

በዚሁ እስር ቤት በርካታ የፖለቲካ እስረኞች ይገኙ እንደነበርና የደረሰ ጉዳት በአግባቡ ሊታወቅ አለመቻሉን የዜና አውታሩ አስነብቧል።

Received on Mon Sep 05 2016 - 17:21:31 EDT

Dehai Admin
© Copyright DEHAI-Eritrea OnLine, 1993-2013
All rights reserved