Ethsat.com: በባህርዳር ሰላማዊ ሰልፈኞች ቦንብ ጭምር ሲወረውሩ ነበር ሲሉ አቶ ጌታቸው ረዳ ገለጹ

From: Berhane Habtemariam <Berhane.Habtemariam_at_gmx.de_at_dehai.org>
Date: Tue, 16 Aug 2016 01:02:37 +0200

በባህርዳር ሰላማዊ ሰልፈኞች ቦንብ ጭምር ሲወረውሩ ነበር ሲሉ አቶ ጌታቸው ረዳ ገለጹ

August 15, 2016

ኢሳት (ነሃሴ 9 ፥ 2008)

Watch these news:

http://video.ethsat.com/?p=27173

http://video.ethsat.com/?p=27152

ESAT Special News Ethiopians Protests Aug 15 2016

http://video.ethsat.com/?p=27127

ሰሞኑን በባህርዳር ከተማና አካባቢ በመንግስት የጸጥታ ሃይሎች ግድያ የተፈጸመባቸው ሰላማዊ ሰልፈኞች በጸጥታ ሃይሎችና በተለያዩ ተቋማት ላይ ሃይል በመጠቀማቸው እርምጃው እንደተወሰደባቸው መንግስት አስታወቀ።

የመንግስት የኮሚኒኬሽን ሚኒስትሩ የሆኑት አቶ ጌታቸው ረዳ ከአልጀዚራ ቴሌቪዥን ጋር ባደረጉት ውይይት በባህር ዳር የተሳተፉ ሰላማዊ ሰልፈኞቹ  በጸጥታ ሃይሎች እና በተቋማት ላይ ቦምብ ጭምር በመወርወራቸው የጸጥታ ሃይሎች የመከላከል እርምጃ ወስደዋል ብለዋል።

የሟቾችን ቁጥር ለመግለጽ ያልፈለጉት አቶ ጌታቸው፣ 30 ሰላማዊ ሰልፈኞች ተገድለዋል የሚለውን የአልጀዚራን ዘገባ አጣጥለዋል ፥ የአልጀዚራ የጋዜጠኞች ስነምግባርም ተጠራጥረዋል።

የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የሰብዓዊ መብት ኮሚሽን በኢትዮጵያ እየተፈጸመ ያለው ግድያ በአለም አቀፍ ገለልተኛ አካል ማጣራት እንዲካሄድበት ሲል ያቀረበን ጥያቄ ለምን የኢትዮጵያ መንግስት እንዳልፈቀደ የተጠየቁት አቶ ጌታቸው ረዳ፣ መንግስት ህዝባዊ አመጽ በተቀሰቀሰባቸው የአማራና ኦሮሚያ አካባቢዎች በችግሩ ዙሪያ ከህዝብ ጋር ሆኖ እየሰራ ስለሆነ የአለም አቀፍ አጣሪ ቡድን አያስፈልገንም ሲሉ ጥያቄውን ውድቅ አድርገዋል።

“ለኢትዮጵያውያን ተጠያቂ የኢትዮጵያ መንግስት እንጂ የአለም አቀፍ ማህበረሰብ አይደለም” ያሉት አቶ ጌታቸው ረዳ፣ መንግስትና ህዝብ ተመካክረው ችግሮቹን ይፈታሉ ሲሉ ተከራክረዋል።

በተጨማሪም ከሳምንት በፊት የኢትዮጵያ መንግስት ለምን የኢንተርኔት አገልግሎትን እንዳቋረጠ የተጠየቁት አቶ ጌታቸው ረዳ፣ የኢትዮጵያ መንግስት የኢንተርኔት የፍሰቱን (ባንድ ዊድዝ) መቀነሱን እንጂ አለማቋረጡን ገልጸው፣ ሆኖም በማህበራዊ መገኛኛ ብዙሃን የተሳሳተ መረጃ ሲሰራጭ እንደነበርና ይህም መቆም እንደነበረበት አብራርተዋል። የአልጀዚራ ጋዜጠኛዋንም ማህበራዊ መገኛኛ ብዙሃን ምን እንደሚሰራ አታውቂም ሲሉ ወርፈዋል።

በኢትዮጵያ ውስጥ ኢንተርኔት መዘጋቱን የኢንተርኔት ትራፊክ የምርመራ ሪፖርት ያቀረበው ኳርትዝ አፍሪካ ድረገጽ በበኩሉ፣ ከሳምንት በፊት የኢትዮጵያ መንግስት ኢንተርኔትን ዘግቶ እንደነበር ሆኖም በሁሉም የአገሪቷ ክፍሎች ይሁን በተወሰኑ አካባቢዎች ማወቅ እንዳልቻለ ገልጿል።

ከቀናት በፊት በባርዳር ከተማ በመንግስት የጸጥታ ሃይሎች በተፈጸመ ግድያ የተገደሉ ሰዎች ቁጥር በከተማዋ ብቻ 55 መድረሱን የከተማዋ ነዋሪዎች ለኢሳት ማስታወቃቸው ይታወሳል።

በአልጀዚራ የተዘጋጀው ውይይት ኢትዮጵያዊው የታሪክ ምሁር ፕሮፌሰር ህዝቅዔል ገቢሳንና የሂውማን ራይትስ ዎች ተመራማሪ የሆኑት ሚስተር ፊሊክስ ሆንር የተሳተፉበት እንደነበር ታውቋል።

*******************************************************************************************

የጎንደር ከተማ ነዋሪዎች ከቤት ያለመውጣት አድማ ለሁለተኛ ቀን ቀጥለው ዋሉ

August 15, 2016

ኢሳት (ነሃሴ 9 ፥ 2008)

ላለፉት ሁለት ሳምንታት ህዝባዊ ተቃውሞን ሲያካሄዱ የቆዩ የጎንደር ከተማ ነዋሪዎች እሁድ የጀመሩትን ከቤት ያለመውጣት አድማ ሰኞ ለሁለተኛ ቀን መቀጠላቸውን የከተማዋ ነዋሪዎች ሰኞ ለኢሳት አስታወቁ።

የከተማዋ ነዋሪዎች የጀመሩትን ይህንኑ ከቤት ያለመውጣት አዲስ አድማ ተከትሎ በከተማዋ የሚገኙ የመንግስትና የግል አገልግሎት መስጫ ተቋማት ሙሉ ለሙሉ ስራ ማቆማቸው ታውቋል።

የከተማዋ አስተዳደር ባለስልጣናት ነዋሪዎች የተለመደ የዕለት ተዕለት እንቅስቃሴያቸውን እንዲቀጥሉ በድምፅ ማጉያ ቅስቀሳን ቢያደርጉም በተቃውሞ የሰነበቱ ነዋሪዎች ምላሽ አለመስጠጣታቸውን ለደህንነታቸው ሲሉ ስማቸውን መግለጽ ያልፈለጉ የጎንደር ከተማ ነዋሪዎች ከዜና ክፍላችን ጋር ባደረጉት ቃለ-ምልልስ አስረድተዋል።

ከተማዋ የተወረረች እንደምትመስል የተናገሩት እማኞች ህዝቡ ራሱን በማስተባበር አዲስ የተቃውሞ ስልፍ መጀመሩን አክለው ገልጸዋል።

ከቤት ባለመዉጣት አድማ ላይ የሚገኙ የጎንደር ከተማ ነዋሪዎች በእለት ተዕለት የተለያዩ ስራዎች ራሳቸውን የሚያስተዳድሩ ሰዎች እንዳይጎዱ በማሰብ ድጋፍ እየሰጡ መሆኑን በዚሁ ድርጊት የተሳተፉ አንዲት ሴት ለኢሳት አስታውቀዋል።

ላለፉት ሁለት ሳምንታት በጎንደርና ባህርዳር ከተሞች እንዲሁም በዙሪያዋ ባሉ አካባቢዎች ህዝባዊ ተቃውሞዎች ሲካሄዱ የሰነበቱ ሲሆን፣ በባህርዳር ከተማ ብቻ 55 ሰዎች በመንግስት የጸጥታ ሃይሎች መገደላቸው ይታወሳል።

ይህንኑ ህዝባዊ ተቃውሞ ተከትሎ የክልሉና የፌዴራል ባለስልጣናት የሃይማኖት አባቶች በማስተባበር ተቃውሞ እንዲረግብ የማግባባት ስራን ሲያካሄዱ እንደቆዩ በተለያዩ ከተሞች የሚገኙ ነዋሪዎች ለኢሳት አስረድተዋል።

ለሁለተኛ ቀን ሰኞ ቀጥሎ ያለው ከቤት ያለመውጣት ተቃውሞ ህዝቡ ያለውን ቁጣ በሰላማዊ መንገድ ለመግለጽ የወሰደው እርምጃ መሆኑን የጎንደር ከተማ ነዋሪዎች ከኢሳት ጋር ባደረጉት ቃለምልልስ ገልጸዋል።

በጎንደር ከተማ ያሉ የመግንስት የጸጥታ ሃይሎች በገዛ ወገኖቻቸው ላይ መተኮስን ትተው የህዝቡን ቅሬታ በአግባቡ እንዲረዱ እጠይቃለሁ ሲሉ አንዲት አዛውንት ለኢሳት ተግረዋል።

የኢትዮጵያ ህዝቡም በዘርና በሃይማኖር ሳይከፋፈል ትግሉን መቀጠል እንዳለበትና የጸጥታ ሃይሎችም ከህዝቡ ጎን መቆም እንደሚገባቸው እኚሁ አዛውንት ከኢሳት ጋር ባደረጉት ቃለምልልስ ጠይቀዋል።

Received on Mon Aug 15 2016 - 17:41:41 EDT

Dehai Admin
© Copyright DEHAI-Eritrea OnLine, 1993-2013
All rights reserved