Goolgule.com: የህወሃት ግፍ እና የሕዝብ ፍጹም ምሬት-የዓይን እማኞች ምስክርነት

From: Berhane Habtemariam <Berhane.Habtemariam_at_gmx.de_at_dehai.org>
Date: Tue, 23 Feb 2016 14:29:12 +0100
tplfpolice

በኦሮሚያ የተማሪዎች ተቃውሞ የተጀመረው በኖቬምበር 12 ቀን 2015 ዓ.ም ጊንጪ በመባል በምትታወቀው ከኢትዮጵያ ዋና ከተማ አዲስ አበባ በስተ ደቡብ ምዕራብ 80 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ በምትገኘው አነስተኛ ከተማ ሲሆን መንስዔውም የመንግስት ባለስልጣን አካላት በአካባቢው የሚገኘውን ደን ለኢንቨስትመንት ልማት በሚል ለመመንጠር በመሞከራቸው ነው፡፡ ተቃውሞው ወዲያው ወደ ሌሎች የኦሮሚያ ክልል አካባቢዎች የተስፋፋ ሲሆን የተቃውሞው ጥያቄም በመስፋት የአዲስ አበባ የተቀናጀ የልማት ማስተር ፕላን በመባል የሚታወቀውን የአዲስ አበባ ማዘጋጃቤት ድንበር የማስፋፋት እቅድ ተቃውሞ ያካተተ ሆኗል፡፡ ተቃውሞው እስከ ዲሰምበር ወር ሲቀጥል ገበሬዎች እና ሌሎችም ተቃውሞውን ተቀላቅለዋል፡፡

በርካታ ተቃውሞ አድራጊዎች እንዳስታወቁት መንግስት ተቃውሞውን በጉልበት ለማስቆም የፈጸመው ተግባር እና በዚህም ምክንያት እየጨመረ የሄደው የሟቾች ቁጥር የተቃውሞውን ትኩረት ተቃውሞ አድራጊዎች ላይ ስለሚፈጸመው ግድያ እና እስር እንዲሁም ለበርካታ አስርት ዓመታት በተፈጸመው ታሪካዊ የኦሮሞ ብሶት ላይ እንዲሆን አድርጎታል፡፡ ኦሮሚያ ለበርካታ ኢትዮጵያዊያን መኖሪያ ናት፤ 35 ሚሊዮን ለሚገመቱ ኦሮሞች አሉ ይኼውም የሃገሪቱ ከፍተኛ መጠን ያለው የጎሳ ቡድን ነው፡፡ በርካታ ኦሮሞች በተከታታይ ጊዜ በነበሩ የኢትዮጵያ መንግስታት መገለል እና መድሎ እንደደረሰባቸው ይሰማቸዋል፡፡ ተቃውሞ የሚያሰማ የኦሮሞ ጎሳ አባል ብዙውን ጊዜ ለእስር እና ለስቃይ ይዳረጋል አሊያም በእስር ላይ ያልተገባ አያያዝ ይፈጸምበታል፣ የኦሮሞ ነጻነት ግንባር አባል ተብሎ ይወነጀላል፤ ግንባሩ በመንግስት ላይ በተውሰነ መልኩ የትጥቅ ትግል የሚያካሂድ እና በሃገሪቱ ፓርላማ አሸባሪ ተብሎ የተመደበ ድርጅት ነው፡፡

በዲሴምበር 16 ቀን ጠቅላይ ሚኒስትር ሃይለማሪያም ደሳለኝ “መንግስት አካባቢውን ለማበጣበጥ ለሚሞክር ማንኛውም ሃይል ላይ ምህረት የለሽ ህጋዊ እርምጃ” እንደሚወስዱ አስታወቁ፡፡ በተመሰሳሳይ ቀን የመንግስት ኮምዩኒኬሽን ጉዳዮች ቢሮ ሚኒስትር አቶ ጌታቸው ረዳ እንዳሉት “ቀውስ እና ብጥብጥ ለመፍጠር ያለመ የተደራጀ እና የታጠቀ የአሸባሪ ቡድን ሞዴል አርሶ አደሮችን፣ የህዝብ አመራሮችን፣ እና ሌሎች በክልሉ የሚኖሩ የሌላ ጎሳ አባላትን መግደል ጀምሯል፡፡” ከዚያ ጊዜ ጀምሮ ወታደራዊ ሰራዊቱን እና የፌዴራል ፖሊሲን ያካተተ የፌዴራል የጸጥታ ሃይል በኦሮሚያ ያለውን የህግ ማስከበር ተግባር እየመራ ይገኛል፡፡

በጃንዋሪ 12 ቀን ኦሮሚያን በመወከል የገዢው ፓርቲ ግንባር አባል የሆነው የኦሮሞ ህዝብ ዴሞክራሲያዊ ድርጅት (ኦህዴድ) በሃገሪቱ የመንግስት ቴሌቪዥን የአዲስ አበባ ማስተር ፕላን እቅድ መሰረዙን አስታወቀ፡፡ ይህ ውሳኔ ያልተጠበቀ የፖሊሲ ለውጥ ቢሆንም ሂውማን ራይትስ ወች ቃለ-መጠይቅ ያደረገላቸው ሰዎች እቅዱ በእርግጥ ያለበት ሁኔታ እና መንግስት መሰረዙ እንደጸና እንዲቆይ ስለማድረጉ አወዛጋቢ ነገሮች አሉ ብለዋል፡፡

ለመጀመሪያ ጊዜ የአዲስ አበባ ማስተር ፕላን በ2014 ዓ.ም. ይፋ ሲሆን በመላ ኦሮሚያ ተቃውሞዎች ተነስተው ነበር፣ ይኼንን ተቃውሞ የጸጥታ ሃይሎች በተኩስ በትነውታል፤ በትንሹ በርካታ በደርዘኖች የሚቆጠሩ ሰዎችም ተገድለዋል፡፡ በመቶዎች የሚቆጠሩ ታስረዋል፡፡ ከታሰሩት ውስጥ በርካታዎቹ ክስ ሳይመሰረትባቸው እንደታገቱ ቆይተዋል፡፡ በ2014 ዓ.ም. ተደርጎ በነበረው ተቃውሞ ታስረው ከነበሩ ሰዎች መካከል ሂውማን ራይትስ ወች ካናገራቸው 25 ያህል ሰዎች በርካታዎቹ በእስር ላይ እንዳሉ የማሰቃየት ተግባር እና ያልተገባ አያያዝ ተፈጽሞባቸዋል፡፡ ቀድሞ ታስረው የነበሩ በርካታ ተማሪዎች ወደ ዩኒቨርቲዎች እንዲመለሱ አልተፈቀደላቸውም፡፡ በዲሰምበር 2 ቀን 2015 ዓ.ም. አምስት የኦሮሞ ተማሪዎች በ2014 ዓ.ም. በነበረው ተቃውሞ በነበራቸው ሚና ምክንያት የጸረ-ሽብር ህጉን በመጣስ ክስ ተመስርቶባቸዋል፡፡ በ2014 ዓ.ም. በነበረው ተቃውሞ ያልተመጣጠነ እና እስከ መግደል የሚያደርስ ሃይል ስለመጠቀሙ በመንግስት  ምንም አይነት የማጣራት ተግባር አላከናወነም፡፡

ማጠቃለያ ግድያዎች፣ አላስፈላጊ እስከ መግደል የሚያደርስ ሃይል አጠቃቀም

በ2015 ዓ.ም. የመጀመሪያዎቹ ሳምንታት በነበሩ ተቃውሞዎች የተቃውሞ ሰልፉን ለመበተን ምላሽ የሰጡት በአብዛኛው የኦሮሚያ ክልል ፖሊሶች ናቸው፣ እነሱም በተቃዋሚዎቹ ላይ አስለቃሽ ጭስ ተጠቅመዋል በአንድ አንድ አጋጣሚዎችም ቀጥታ ወደተቃውሞ አድራጊዎቹ የተኮሱበት ጊዜ አለ፡፡ በመጀመሪያ ላይ አብዛኛዎቹ ግድያዎች እንደተፈጸሙ የተመዘገበው በምሽት ሲሆን ይኼውም የጸጥታ ሃይሎች ቤት ለቤት ተቃውሞ አድራጊዎቹን በማደናቸው ነው፡፡ የተወሰኑ ተማሪዎችን ለማምለጥ ሲሞክሩ የገደሏቸው ሲሆን የተቀሩትን በሚታሰሩበት ወቅት በተነሳ አምባጓሮ ነው የተገደሉት ሆኖም የበርካቶቹ ሞት ትክክለኛ ምክንያት አልታወቀም፡፡

በዓለም ዓቀፍ የሰብዓዊ መብቶች መስፈርት መሰረት የህግ አስከባሪ አካል እስከ መግደል የሚያደርስ ሃይል መጠቀም ያለበት ራስን ለመከላከል ወይንም በሌሎች ሰዎች የህይወት ላይ አደጋ የሚያመጣ ከሆነ ነው፡፡

የሃገሪቱ ጠቅላይ ሚኒስትር በዲሴምበር 16 ቀን “መንግስት አካባቢውን ለመበጥበጥ የሚሞክሩ ማንኛውም ሃይሎች ላይ ምህረት የለሽ ህጋዊ እርምጃ ይወስዳል” ካሉ በኋላ የአይን እማኞች እንደገለጹት የፌዴራል ፖሊስ እና ወታደራዊ ሰራዊት ከኦሮሚያ ክልል ፖሊስ ጋር በጋራ እንዲሰሩ በመላ ኦሮሚያ ተሰማሩ፡፡ በርካታ ተቃውሞ አድራጊዎች እንደገለጹት የፌዴራል ፖሊስ እና ወታደሮች ቀጥታ የተቃውሞ ሰልፍ የሚያደርጉ ሰዎች ላይ ተኩሰዋል፡፡

ከምዕራብ ሸዋ የ17 ዓመቱ የተቃውሞ አድራጊ ዋቆ – ስሙ እንደሌሎቹ ሁሉ ለደህንነቱ ሲባል የተቀየረ – ለውጡን እንደሚከተለው አብራርቶታ፤

በተቃውሞው የመጀመሪያ ወቅቶች (በኖቬምበር አጋማሽ) የኦሮሚያ ፖሊስ ወደየቤታችን እንድንመለስ ሊመክረን ሞክሯል፡፡ ተቃወምናቸው ስለዚህ በአስለቃሽ ጋዝ ሰልፉን በተኑት እና በርካቶችን አሰሩ፡፡ ከበርካታ ቀናት በኋላ ሌላ ተቃውሞ አደረግን፡፡ በዚህ ወቅት እነሱ (የፌዴራል ፖሊስ) መጡ፡፡ በርካታ ጥይቶችን ወደ ሰማይ ተኮሱ፡፡ ህዝቡ ሊበተን ስላልቻለ አስለቃሽ ጭስ ተኮሱ እናም በዚህ ግር ግር ላይ እያለን የጥይት ድምጾችን መስማት ጀመርን ከእኔ ጎን የነበሩ ተማሪዎችም ባሉበት መውደቅ ጀመሩ፡፡ ጓደኛየ (ስሙ ያልተጠቀሰ) በጥይት ተመቶ ተገደለ፡፡ እሱን ለመግደል ኢላማ ተደርጎ አልነበረም፤ ወደ ተሰበሰበው ህዝብ ቀጥታ በዘፈቀደ ነበር የሚተኩሱት፡፡

ከአርሲ ነገሌ የ16 ዓመት እና የ10ኛ ክፍል ተማሪ የሆነው ጉዲና ደግሞ በዲሰምበር መጀመሪያ አካባቢ በነበረው ተቃውሞ የባለስልጣን አካላቱን ምላሽ እንደሚከተው አብራርቷል፤

ሁሉም ትምህርት ቤቶች በአንድ ላይ ሆነው በህብረት ወደ አደባባይ ወጡ፡፡ ተቃውሞ እያደረግን ባለንበት ወቅት አስለቃሽ ጭሶች ተወረወሩ፣ እኛ ጉዟችንን ቀጠልን ከዚያም ከኋላችን የጥይት ተኩስ ሰማን፤ በርካታ ተማሪዎች ተመተው የስቃይ ድምጽ እያሰሙ ወደቁ፡፡ አንድ በጣም ወጣት የእኔ ትምህርት ቤት ልጅ ጉሮሮው ላይ ተመቶ ደም በብዛት ሲፈስ አይቻለሁ፡፡ ሁልጊዜ ማታ ይህ ተማሪ በህልሜ ይመጣብኛል፡፡

በተለይ ከዲሴምበር አጋማሽ ጀምሮ በዋናነት የፌዴራል ፖሊስን ያካተተው የጸጥታ ሃይል ወደተቃውሞ ሰልፍ አድራጊዎቹ ቀጥታ መተኮሱን በማስመልከት በአርሲ፣ ምዕራብ ሸዋ እና ምስራቅ ወለጋ ዞኖች የነበሩ ተቃውሞ አድራጊዎች ተመሳሳይ ክስተቶችን አስረድተዋል፡፡ አስለቃሽ ጭስ ሲጠቀሙ እና ቀጥታ ወደ ህዝቡ ጥይት ሲተኩሱ ያለምንም ቅድመ ማስጠንቀቂያ አሊያም ያለበቂ ቅድመ ማስጠንቀቂያ ነው፡፡

በተለያየ ጊዜ ቃለ-መጠይቅ የተደረገላቸው ሶስት የሁለተኛ ደረጃ ተማሪዎች ከአርሲ አንድን ክስተት እንደሚከተለው አብራርተዋል፡፡ የ17 ዓመቱ ኩማ እንዳለው፤

የስድሰተኛ ክፍል ተማሪ እንደተገደለ ሰማን (በጎረቤታማ መንደር)፡፡ ወንድማማችነታችንን ለማሳየት ስንል ተቃውሞ ለማድረግ ወሰንን፡፡ የተለያዩ ትምህርት ቤቶች በጋራ ተሰባስበን ወደ መንግስት መስሪያ ቤቶች መዝመት ስንጀምር የጸጥታ ሃይሎች ወደ እኛ መምጣት ጀመሩ፡፡ አስለቃሽ ጭስ ወረወሩ ከዚያም የጥይት ተኩስ ድምጽ ሰማን፡፡ ጓደኛዬ (ስሙ ያልተገለጸ) ደረቱ ላይ ተመታ፡፡ እየደማ ሲወድቅ አይቸዋለሁ፡፡ እየሮጥን ተመለስን ወደኋላ ዞሬ አላየሁም፡፡ እናቱ በኋላ ጓደኛዬ እንደተገደለ ነገረችኝ፡፡ 17 ዓመቱ ነበር፡፡

ተቃውሞ የማድረግ መታቀዱን ተከትሉ ለመሳተፍ ያላቸውን ተስፋ ለማጨናገፍ የጸጥታ ሃይሎች በሻሸመኔ የሚገኝ አንድ ትምህርት ቤት ቅጥር ግቢ ውስጥ ገብተዋል፡፡ የ9ነኛ ክፍል ተማሪ የሆነው የ17 ዓመቱ ገመዳ የሚከተለውን ብሏል፤

ተቃውሞ ለማድረግ እቅድ ነበረን፡፡ በጧት 2 ሰዓት የኦሮሚያ ፖሊስ በትምህርት ቤቱ ቅጥር ግቢ መጣ፡፡ አራት ተማሪዎችን አሰሩ (ከ9-11ኛ ክፍል) የቀረነው ሌሎቻችን ነገሩ ስላበሳጨን ፖሊሶቹ ላይ መጮህ ጀመርን፡፡ አንዱ ፖሊሶቹ ላይ ድንጋይ ወረወረ እናም ፖሊሶቹ በፍጥነት ከግቢው ወጥተው በመሄድ ከአንድ ሰዓት በኋላ ከፌዴራል ፖሊስ ጋር ተመልሰው መጡ፡፡ ቀጥታ ወደ ግቢው በመግባት ሶስት ተማሪዎችን በጥቁር ጠመንጃ ተኩሰው ገደሉ፡፡ ፊታቸው ላይ ነበር የተመቱት እና ተገድለዋል፡፡ አስከሬናቸውን ይዘው ሄዱ፡፡ ጧቱን ሙሉ በየክፍላችን እንድንቆይ አደረጉን እና ቀትር ላይ ተመልሰው በመምጣት እኔን ጨምሮ 20 የምንሆን ተማሪዎችን ወሰዱን፡፡

ዘፈቀዳዊ እስር እና እገታ

በበርካታ ደርዘኖች የሚቆጠሩ ሰዎች ለሂውማን ራይትስ ወች እንደተናገሩት ያለ በቂ መሰረት ጓደኞቻቸው አሊያም የስራ አጋሮቻቸው ታስረዋል፤ በርካታዎቹ ታሳሪዎች የገቡበት ቦታ አልታወቀም፡፡ ከተለያዩ ኦሮሚያ አካባቢዎች የተውጣጡ አስራአምስት ተቃውሞ አድራጊዎች በራሳቸው ላይ የደረሰውን እስር አብራርተዋል፡፡ በቀን ከተከናወነ የተቃውሞ ሰልፍ በኋላ ሁልጊዜ በምሽት የጸጥታ ሃይሎች ቤት ለቤት በመዘዋወር በተቃውሞ ሰልፉ ታሳትፎ ያላደረጉ ተማሪዎችን ጭምር የሚያስሩ ሲሆን በጃንዋሪ 9 ቀን በቦረና ዞን አንድ የ 8 ዓመት ታዳጊ ጭምር አስረዋል፡፡ የመጀመርያ አላማቸው አዋቂ እና ወጣት ወንዶችን ነው ሆኖም በርካታ ሴቶች እና ልጃገረዶችም ጭምር ታስረዋል፡፡ የተያዙ ሰዎች ወደ ፖሊስ ጣቢያ፣ ወታደራዊ ካምፕ እና ጊዜያዊ የማቆያ ማዕከል ይወሰዳሉ፡፡

ከቦረና ዞን የ7ተኛ ክፈሉ ኩማ በዲሴምበር ወር መጀመሪያ አካባቢ ታስሮ ነበር፤ ባልታወቀ ስፍራ ለአምስት ቀናት ተይዞ የቆየ ሲሆን በእንጨት ብትር ተደብድቧል፡፡

“ለምን የተቃውሞ ሰልፉ ውስጥ ገባህ? መንግስትን ትጠላለህ ማለት ነው? ለምን? መልካም ነገር አላደረግንልህም?” ብለው ጠይቀውኛል፡፡ ከዚያም ከኦነግ (መንግስት በአሸባሪ ቡድንነት የፈረጀው የኦሮሞ ነጻነት ግንባር) ጋር ግንኙነት እንዳለኝ መናገር ጀመሩ፡፡ የተቃውሞ ሰልፉ ከኦነግ ጋር ምን የሚያገናኘው ነገር እንዳለ ጠየቁኝ፡፡ ከአንድ ሰው በላይ ተጨማሪ ሰው ጋር ህዝብ ወደሚሰበሰበበት ቦታ እንደማልሄድ ቃል የገባሁበትን ወረቀት ካስፈረሙኝ በኋላ ለቀቁኝ፡፡ ከበርካታ ቀናት በኋላ ሌላ ተቃውሞ ነበረ፤ በዚህኛው ተቃውሞ አልተሳተፍኩም ሆኖም ልታሰር እንደምችል አውቅ ነበር፡፡ የተኩስ ድምጾችን እየሰማሁ ቤት ቁጭ ብየ ዋልኩ ሙሉ ቀን፤ የሚገደሉት ሰዎች የማላውቃቸው እንዲሆኑ ተስፋ እያደረኩ ነበር፡፡

የ7ተኛ ክፍሉ ተማሪ ገመዳ የተቃውሞ ሰልፍ ለማድረግ በታቀደበት ቀን በትምህርትቤቱ ግቢ እያለ ታስሮ እንደነበር ተናግሯል፡

ለ10 ቀናት በፖሊስ ጣቢያ ተይዤ ቆይቻለሁ፡፡ ለመጀመሪያዎቸሁ ሶስት ቀናት ሁልጊዜ ማታ ማታ በእንጨት በትር ጀርባየን እና እግሬን ይደበድቡኝ ነበር፣ እንዲሁም ከተቃውሞው ጀርባ ማን እንዳለ እና የኦነግ አባል እንደሆንኩ ይጠይቁኝ ነበር፡፡ ከተፈታሁ ከበርካታ ሳምንታት በኋላ ተቃውሞ በከተማዋ እንደገና ተጀመረ፡፡ ደግመው አሰሩኝ፡፡ ተመሳሳይ ድብደባ እና ተመሳሳይ ጥያቄዎች ነበሩ፡፡ ቤተሰቤ ለፖሊስ ጉቦ በመክፈል እንድፈታ አደረጉኝ፡፡

የባለስልጣን አካላቱ የተቃውሞ ሰልፍ አድራጊዎቹን እንደረዱ የተገለጹ ሰዎች ላይ የጋራ ቅጣት ጥለዋል፡፡ በዲሴምበር መጀመሪያዎቹ አካባቢ በአርሲ ከጸጥታ ሃይሎች ያመልጡ የነበሩ ተቃውሞ አድራጊ ተማሪዎችን እንደረዳች የታወቀባት ሌሊሳ እንዳለችው፡

ተቃውሞውን አልተቀላቀለኩም ሆኖም የተኩስ ድምጽ ሙሉ ቀን እና ማታም ጭምር እሰማ ነበር፡፡ ተማሪዎች ወደአገኙት ቦታ እየሮጡ ራሳቸውን ለመደበቅ ይሞክሩ ነበር፡፡ አስር ተማሪዎች ወደ እኔ መጡ እና እንድደብቃቸው እርዳታን ስለጠየቁ ከፖሊስ እንዲደበቁ አደረኩ፡፡ ፖሊስ በምሽት ከቤት ለቤት በመንቀሳቀስ ተማሪዎችን ያስር ነበር፡፡ ወደቤቴ መጡ እና ሁሉንም ወንዶች አሰሯቸው እኔም የቀሩት ሶስቱ ሴቶች ልጆቼ መሆናቸውን አሳመንኳቸው፡፡ ከዚያም ከአንድ ሰዓት በኋላ ተመልሰው መጥተው ባለቤቴን አሰሩት፡፡ እኔ ፊት ደብድበውታል፣ እንዳይገድሉት ስለምናቸው እኔን በያዙት ጠመንጃ በሰደፍ መቱኝ፡፡ ባለቤቴን ይዘውት ሄዱ፤ ከዚያን ጊዜ ጀምሮ ስለእርሱ የሰማሁት ነገር የለም፡፡

የግል ትምህርት ቤት ባለቤት የሆነው ነጋሱ የእርሱ ትምህርትቤት ተማሪዎች በተቃውሞው ስለተሳተፉ መታሰሩን አመልክቷል፡

የግል ትምህርት ቤት አለኝ (ቦታው ያልተጠቀሰ)፡፡ ተማሪዎቹ አመጹ ሆኖም ፖሊስ ሰልፉን በጉልበት አልበተነውም ይልቁንስ በፊልም ሲቀርጹ ቆይተው ማታ ላይ ብዙ ሰዎችን አሰሩ፡፡ ከታሰሩት ውስጥ አራቱ ተቃውሞ አድራጊዎች ከኔ ትምህርት ቤት ነው፡፡ ስለዚህ ፖሊስ በማታ ቤቴ መጥቶ አሰረኝ እኔንም እና ወደ ጦር ካምፕ ወሰዱኝ (ስሙ ያልተገለጸ)፡፡ ለአምስት ቀናት ያህል ብቻዬን አንድ ጨለማ ጉድጓድ ውስጥ ተይዤ ቆየሁ፡፡ በጣም ቀዝቃዛ ነበር ለሁለት ቀናትም ምንም አይነት ምግብ አልሰጡኝም፡፡ ማታ ማታ ይደበድቡኝ ነበር እንዲሁም የኦሮሞ ፌዴራሊስት ንቅናቄ እና ኦነግ ለተባሉት የተቃዋሚ ቡድኖች የገንዘብ እርዳታ እንደሰጠሁ ይወንጅሉኝ ነበር፡፡ እንዲሁም በማህበራዊ ድረ-ገጽ ቪድዮዎችን ለጥፈሃል እና ለኦ ኤም ኤን ልከሃል ብለው ወንጅለውኛል፡፡ ዝምብለው ነበር ይኄን የሚሉት፡፡ ትምህርትቤቴን እንዲዘጋ ካደረጉ በኋላ የባንክ አካውንቴን እንዳይንቀሳቀስ አደረጉት፡፡ ቤቴንም ወስደውብኛል፡፡ አሁን ምንም የለኝም ተማሪዎቹም እኔ በማቆያ ቦታዎች  ያለፍኩበትን መንገድ እያለፉበት ነው  አሊያም ትምርት ቤቶቹ ስለተዘጉ ወደ ትምህርት ቤት መሄድ አልቻሉም፡፡

ተናጋሪ እንደሆኑ የሚታወቁ ተማሪዎች እና ከቤተሰባቸው አባላት ውስጥ የተቃውሞ ፖለቲካ ታሪክ እንዳላቸው የሚታወቁ ተማሪዎች የበለጠ አደጋ ላይ ናቸው፡፡ የ25 ዓመቱ ሌንጮ እንዳለው:-

በጣም ተናጋሪ እንደሆንኩ እና የተማሪዎች መሪ እንደሆንኩ እታወቃለሁ፡፡ አባቴም ቢሆን መንግስትን በመቃወም የታወቀ ነው፡፡ ስለሰጋሁ በተቃውሞ ሰልፉ እንኳን አልተሳተፍኩም ነበር ነገር ግን ተቃውሞውን እንዳስተባበርኩ ተደርጎ ተለይቻለሁ፡፡ ታስሬ ነበር እና ወደ ፖሊስ ጣቢያ ስወሰድ የአካባቢው ባለስልጣናት፣ የኦሮሞ አርቲስት (ዘፋኝ) መምህሮቼን እና በሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ያሉ በተናጋሪነታቸው የሚታወቁ ሁሉንም ተማሪዎች አይቻቸዋለሁ፡፡ ተጽዕኖ ፈጣሪ ናቸው ብለው የገመቷቸውን በሙሉ እያሰሩ ነበር የሚገኙት፡፡ ሁሉም ስጋት ስለነበራቸው የተቃውሞ ሰልፉን ተቀላቅለው ነበር ብዬ ለመገመት ይከብደኛል፡፡

በሃገሪቱ በህግ የተመዘገበውን የኦሮሞ ፌዴራሊስት ኮንግረስ አባላትን ጨምሮ ታዋቂ የኦሮሞ ምሁራን ጭምር ታስረው ነበር፡፡ በዲሰምበር 23 ቀን ምክትል ሊቀ መንበሩ በቀለ ገርባ ከቤቱ ተይዞ ማሰቃየት እና ያልተገባ የእስረኞች አያያዝ እንደሚጸምበት ወደሚታቀው አዲስ አበባ የሚገኘው ማዕከላዊ እስር ቤት ተወስዷል፡፡ በጃንዋሪ 22 ቀን ፍርድቤ የቀረበ ሲሆን በአፋኙ የጸረ-ሽብር ህግ መሰረት ምርመራ እየተደረገባቸው መሆኑን በመግለጽ አቃቢ ህግ ለተጨማሪ የምርመራ ጊዜ 28 ቀናት ተሰጥቶታል፡፡ በቀለ በኦሮሚያ ፖለቲካ ውስጥ ለዘብተኛ ድምጽ ያለው ተቃዋሚ ሲሆን አመጻ አልባ ተቃውሞን በሙሉ እምነት ሚደግፍ እና የሚያበረታታ ነው፡፡

በተቃውሞው በንቃት እንደሚሳተፉ ከተገለጹት ሰዎች በተጨማሪ የፀጥታ ሃይሎች ሌሎች ተጽዕኖ ፈጣሪ ሰዎችንም አስረዋል፤ ከእነዚህም ወስጥ ታዋቂ የኦሮሞ ነጋዴ ሴቶች፣ መምህራን፣ ፕሮፌሰሮች፣ እና በርካታ ዘፋኞች እና አርቲስቶች ይገኙበታል፡፡ አንድ መምህር እንዳለው፡

ተማሪዎቹ ተቃውሞ አስነስተዋል፡፡ በማታ መጥተው በርካቶችን አሰሯቸው፤ የኔ ተማሪዎች ማታ ላይ ደውለውልኝ ፖሊስ ሊያስራቸው በራቸው ላይ እንደሚገኝ ገልጸውልኛል፡፡ ከዚያም በርካቶቹ መምህራንም እንደታሰሩ ሰማሁ፡፡ በዛ ምሽት ከከተማ ውጭ ነበርኩ፡፡ ከዚያም የወረዳው አስተዳዳሪ ደወለልኝ እና ላስቆማቸው ስላልቻልኩ ለተማሪዎቼ ተግባራት እኔ ተጠያቄ እንደሆንኩ ገለጸልኝ፡፡ እኔ ከመጀመሪያውም የአዲስ አበባን ማስተር ፕላን መተግበር እና አንዴት ተማሪዎቹን ይህ እቅድ ለእነሱ ጥሩ እንደሚሆን ለማሳመን በተመለከተ በሚደረግ ውይይት ላይ ለመሳተፍ ፈቃደኛ ስላለሆንኩ ቀድሞውንም ችግር ላይ ነበርኩ፡፡

አሁን በስደት ላይ የሚገኝ አንድ ታዋቂ ኦሮሞ ዘፋኝ የሚከተለውን ብሏል፡

አንድ ዘፈን በዩቲዩብ ለቀኩ (በዲሰምበር ወር) ዘፈኑም ስለተቃውሞው የሚናገር እና ተማሪዎች ዝምታውን በመስበር በህዝባችን ላይ እየደረሰ ያለውን ጥቃት ይፋ እንዲያወጡት የሚገልጽ ነው፡፡ ከዚህ በፊት በዘፈኖቼ ምክንያት ለሶስት ጊዜያት ታሰሬ አውቃለሁ፡፡ ዘፈኖቼ የኦሮሞ ታሪክ አና ባህል ላይ ያጠነጠኑ ናቸው ሆኖም ፖለቲካዊ ይዘት እንዳላቸው እንዳይታወቁብኝ እጠነቀቅ ነበር፡፡ ሆኖም አሰሩኝ፡፡ ለስስተኛ ጊዜ ካሰሩኝ በኋላ ግን በራሴ ላይ የማደርገውን ቅድመ-ምርመራ በማቆም በግልጽ ሙዚቃዬ ላይ የምፈልገውን መልዕክት ማስተላለፍ ጀመርኩ፡፡ ሙዚቃዬ ከተለቀቀ ከአንድ ሰዓት በኋላ ከአካባቢው አስተዳዳሪ ሊያስሩኝ እንደሆነ ስለተነገረኝ ቤቴን ጥዬ ሸሸሁ ከዚያም በኋላ ተመልሼ አላውቅም፡፡

በጃንዋሪ 2016 ዓ.ም. አንድ ኢትዮጵያ ደህንነት ባለስልጣን ለሂውማን ራይትስ ወች በህዝብ ዘንድ ተቀባይነት ያላቸውን ሰዎች መከታተል የመንግስት ፖሊሲ መሆኑን አረጋግጧል፡፡ “የተከበሩ ኦሮሞዎች ላይ የተለየ ትኩረት ማድረግ ጠቃሚ ነው” ብሏል፡፡ “እንደ በቀለ አይነቶቹን ጨምሮ ከከፍተኛ ደረጃ እስከ መምህራን፣ ተቀባይነት ያላቸው ተማሪዎች እና ኦሮሞ አርቲስቶችን ጨምሮ ማንኛውም ኦሮሞዎችን ማስተባባር የሚችል ሰው የተለየ ትኩረት ይደረግበታል፡፡”

ሂውማን ራይትስ ወች በ2014 ዓ.ም. ታስረው የነበሩ እና ቆይተው የተለቀቁ መልሶም ከእንደገና በቅርቡ በኖቬምበር 2015 ዓ.ም. ተቃውሞው ሲጀመር ወዲያው ታስረው የነበሩ በርካታ ቁጥር ያላቸው ተማሪዎችን ቃለ-መጠይቅ አድርጓል፡፡ የተወሰኑት በእስር ቤቶች ያለውን ዘግናኝ አያያዝ ገልጸዋል፡፡ በወቅቱ የሁለተኛ ዓመት ተማሪ የነበረው ዋይሲራ እንዳለው፡-

(በ2014 ዓ.ም.) ለሁለት ሳምንታት ያህል ታስሬ ነበር፡፡ በፓንት ብቻ ሆኜ ራቁቴን እንድቆም ተደርጌ በዱላ ይደበድቡኝ ነበር፡፡ በጀርባየ ላይ የኤሌክትሪክ ገመድ አስረዋል፡፡ ኦነግ እንደሆንኩ እንዳምን እና ከኦነግ ጋር ነው ብለው የጠረጠሩት ወንደሜ ኦነግ ጋር እንደሆነ እንዳምን ነበር የፈለጉት፡፡ ከጊዜ በኋላ ተፈታሁ፡፡ ወደ ትምህርት ቤት ተመልሼ እንድሄድ አልተፈቀደልኝም፤ ስለዚህ ምንም ሳልሰራ ቁጭ ብየ ነበር የምውለው፡፡ ቤተሰቦቼ ወደሚገኙበት መንደር ተመለስኩ፡፡ በኦሮሚያ ተቃውሞው እንደገና ሲጀመር ያለሁበት ቤት ድረስ መጥተው ከእንደገና አሰሩኝ፡፡ በአካባቢው ምንም አይነት ተቃውሞ አልነበረም ነገርግን ቀድሞ በነበርኩበት እና በታገድኩበት ዩኒቨርስቲ ግቢ ውስጥ ተቃውሞ ተነስቶ ነበር፡፡ ተማሪዎቹን በማነሳሳት ወነጀሉኝ እናም ለሁለት ቀናት ያህል ደብድበውኛል፡፡ ከዚያም ከእስር ተፈታሁ፡፡ ምናልባት ተቃውሞ ለማስነሳት ያስባሉ ብለው የገመቷቸውን ማንኛውንም ሰዉ ላይ ትኩረት አድርገው ነበር፡፡

በእስር ቤቶች ማሰቃየት እና ያልተገባ አያያዝ

ሁሉም ቃለ-መጠይቅ ተደርጎላቸው የነበሩ ታስረው የነበሩ ተማሪዎች በተቃውሞው ጀርባ ማን እንዳለ እንዲገልጹ እና ስለቤተሰባቸው ታሪክ ተጠይቀው እንደነበረ ገልጸዋል፡፡ ተማሪዎቹ እንዳሉት መርማሪዎቹ ከተቃዋሚ ድርጅቶች ጋር ግንኙነት እንዳላቸው ወንጅለዋቸዋል – በዋናነት በህግ ከተመዘገበው የኦሮሞ ፌዴራሊስት ኮንግሬስ እና ከኦሮሞ ነጻነት ግንባር ጋር ግንኙነት አላችሁ ብለው ነው የወነጀሏቸው፡፡ የተወሰኑ ተማሪዎች ለዲያስፖራ ዓለም ኣቀፍ መገናኛ ብዙሃን መረጃ አቀብላችኋል ተብለው በመርማሪዎች የተወነጀሉ ሲሆን በርካታ ቁጥር ያላቸው የተማሪዎች ስልኮች፣ የፌስቡክ ገጽ፣ እና ኢሜይል አድራሻ በታሰሩባቸው ወቅቶች ተመርምረዋል፡፡ እነዚህ መርማሪዎችን በተመለከተ የተደረጉ ማብራሪያዎች ሂውማን ራይትስ ወች ለበርካታ ዓመታት ኦሮሚያን በተመለከተ ከመዘገባቸው መረጃዎች ጋር ተመሳሳይነት አላቸው፡፡

በአዳማ ዩኒቨርሲቲ መጀመሪያ ዓመት ተማሪ ሆነው ቶሎሳ የሚከተለውን ብሏል፡

ከተቃውሞው በኋላ ምሽት ላይ ነበር፤ በወቅቱ ከነበረው አስለቃሽ ጭስ እያገገምን ባለበት ወቅት እና በተቃውሞው ወቅት ማን በጥይት ተመቶ እንደነበር ለመለየት ጥረት በምናደርግበት ወቅት ነው የጸጥታ ሃይሎች የማደሪያ ቦታችንን ያጥለቀለቁት፡፡ እኔ ካለሁበት ቦታ 17 የምንሆን ተማሪዎችን አይናችንን ካሰሩን በኋላ ለሁለት ሰዓታት ያህል በመኪና ከከተማ ውጭ ይዘውን ተጓዙ፡፡ ለዘጠኝ ቀናት ያህል ስራው ያላለቀ አዲስ ህንጻ ውስጥ አስቀመጡን፡፡ ሁልጊዜ ማታ ማታ አንድ በአንድ ይዘውን እየወጡ በዱላ ይደበድቡን እና ይገርፉን ነበር እንዲሁም ከተቃውሞው ጀርባ ማን እንዳለ እና የኦነግ አባላት ስለመሆናችን ይጠይቁናል፡፡ እኔ ኦነግ ማን እንደሆነ እንኳ እንደማላውቅ እና ህዝብን በዚህ መልኩ ማሰቃየት ግን ሁሉንም ወደ ኦነግ ጎራ እንዲቀላቀሉ እንደሚያደርግ ነገርኳቸው፡፡ ይኼንን ስላልኩ በሃይል ደበደቡኝ፡፡ ሙሉ ሌሊቱን የስቃይ ድምጽ ስንሰማ እናድራለን፡፡ ወደ መጸዳጃ ቤት ስንገባ ተማሪዎች በወገባቸው ተንጠልጥለው ኮርኒስ ላይ ታስረው እየተገረፉ አይቻለሁ፡፡ አንድ መቶ የሚሆኑ ተማሪዎችን አይቻለሁ፡፡ መርማሪዎቹ ከእኛ አካባቢ አልነበሩም፡፡ አማርኛ እንድንናገር ያስገድዱን ነበር (የሃገሪቱ ብሔራ ቋንቋ)፡፡ ኦሮምኛ ስንናገር ይበሳጩ እና ይደበድቡን ነበር፡፡

በ20ዎቹ እድሜ ክልል የምትገኘው መቲ በምስራቅ ወለጋ ተቃውሞ ከተካሄደ ከአንድ ቀን በኋላ የኦሮሞ ባህላዊ አልባሳትን ስትሸጥ ተገኝታ በዲሰምበር ወር መጨረሻዎቹ አካባቢ ታስራ ነበር፡

ታስሬ ለአንድ ሳምንት ያህል በፖሊስ ጣቢያ እንደቆይ ተደርጌያለሁ፡፡ ሁልጊዜ ማታ ማታ ጎትተው ያወጡኝ እና በደረቅ እንጨት እና በባለጎማ ብትር ይደበድቡኝ ነበር፡፡ ከዚያም ወደ ሌላ ቦታ ወሰዱኝ (ቦታው ያልተገለጸ)፡፡ ለብቻየ አስረው አቆዩኝ፡፡ በተለያዩ ሶስት አጋጣሚዎች ልብሶቼን እንዳወልቅ ተገድጄ በፖሊስ መኮንኖቹ ፊት እንድንቀሳቀስ የተደረኩ ሲሆን ከኦነግ ጋር ስላለኝ ግንኙነት ይጠይቁኝ ነበር፡፡ ተቃውሞውን በማደራጀት በኩል ተባባሪ እንደነበርኩ ካላመንኩ ሊገሉኝ እንደሚችሉ ያስፈራሩኝ ነበር፡፡ ለምን የኦሮሞ አልባሳትን እና ጌጣጌጦችን እሸጥ እነደነበር ጠይቀውኛል፡፡ የማካሂደው ንግድ በኦሮሞነት ከመኩራት የመነጨ መሆኑን ነግረውኝ ሰዎችም ወደ አደባባይ ለሰልፍ የሚወጡት በዚሁ ምክንያት መሆኑን አስታወቁኝ፡፡ በመጀመሪያ በጨለማ ክፍል ውስጥ ነበርኩ፤ ከዚያም በተቃውሞው ወቅት ታስረው ወደነበሩ ሌሎች ሴቶች ጋር ተቀላቅዬ ቆየሁ፡፡

በቦረና ዞን ውስጥ የምትገኝ አንድ የ22 ኣመት ሴት ለሂውማን ራይትስ ወች እንደገለጸችው በዲሰምበር ወር ማገባደጃ አካባቢ ተቃውሞ በተደረገበት እለት ምሽት ታስራ ነበር፤ እናም የወታደራዊ ካምፕ እንደሚመስል በገለጸችው ቦታ ተወስዳለች፡፡ ብቻዋን ሙሉ ለሙሉ ጨለማ በሆነ ቦታ ታስራ ቆይታለች፡፡ ለሁለት ሳምንታት በዚህ ሁኔታ በቆየችባቸው ወቅቶች ባልታወቁ ሰዎች ለሶስት ጊዜያት ተደፍራለች፡፡ በያንዳንዱ አጋጣሚ ሁለት ሁለት ሰዎች እንደነበሩ ገልጻለች፡፡ በተደጋጋሚ ከታሰረችበት ክፍል ተጎትታ እየወጣች በተቃውሞው ላይ ያላትን ተሳትፎ ትጠየቅ ነበር፤ ሁለቱ ወንድሞቿ ያሉበትንም አድራሻ ይጠይቋታል፤ መርማሪዎቹ ወንድሞቿ የተማሪዎችን አመጽ እየቀሰቀሱ እንደሆነ ወንጅለዋቸዋል፡፡ ሁለቱን ወንድሞቿን ለጥያቄ ወደ ጸጥታ ሃይሎቹ እንደምታመጣቸው ቃል በመግባት በቅድመ-ሁኔታ ተፈታለች፡፡

የጤና እና የትምህርት አገልግሎት የማግኘት መብት

ባለስልጣን አካላቱ የጤና ባለሙያ ሰራተኞችን ለማሰር ልዩ ትኩረት አድርገውባቸዋል በዚህም ምክንያት የተወሰኑ የቆሰሉ ተቃውሞ አድራጊዎች የህክምና እርዳታ ማግኘት አልቻሉም፡፡ በምስራቅ ወለጋ ተማሪ የሆነው ደመቅሳ እንደገለጸው በዲሰምበር ወር ማገባደጃ ላይ የኦሮሚያ ክልላዊ ፖሊስ በተቃውሞ አድራጊዎች ላይ በተኮሰው አስለቃሽ ጭስ ምክንያት እና ተገፍቶ በመውደቁ በክንዱ እና ፊቱ ላይ ለደረሰበት ጉዳት የህክምና እርዳታ ማግኘት ተከልክሏል፡፡ “እነሱ (የጤና ባለሙያዎቹ) እንዳሉት እኔን ማከም አይችሉም፡፡ ከአንድ ቀን በፊት የጸጥታ ሃይሎች ሁለት የስራ አጋሮቻቸውን በተቃውሞ ላይ ለነበሩ ሰዎች የህክምና እርዳታ ስላደረጉ አስረዋቸዋል፡፡ ለተቃዋሚዎች የጤና አገልግሎት ሽፋን በመስጠት በሚል ተወንጅለዋል፡፡”

የተቃውሞው ምልክት የሆነውን ሁለት እጃቸውን ከራስ በላይ ከፍ አድርጎ ክንድ እና ክንዳቸውን በመስቀለኛ መንገድ በማጣመር ፎቶ ተነስተው በፌስቡክ ማሕበራዊ ደረ-ገጽ በመልቀቃቸው ምክንያት የጸጥታ ሃይሎች እንዳስፈራሯቸው እና እንዳሰሯቸው የጤና ባለሙያዎች ገልጸዋል፡፡ በምስራቅ ወለጋ የሚገኝ አንድ የጤና ባለሙያዎች እንደገለጸው በርካታ ተማሪዎች በጥይት ተመተው ከፍተኛ እርዳታ በሚስፈልጋቸው ወቅት የአንድ ወታደር አነስተኛ ጉዳትን እንዲያክም ጠመንጃ ደቅነው አስገድደውታል፡፡ በዛው እለት ምሽት ቢያንስ አንድ ተማሪ በደረሰበት ጉዳት ሳቢያ እንደሞተ የጤና ባለሙያው ተናግሯል፡፡

በርካታ ተማሪዎች እንዳሉት የአካባቢው ባለስልጣናት ትምህርትቤቶችን እንዲዘጉ ያደረጉ ሲሆን ይኼውም ተማሪዎቹ ለተቃውሞ እንዳይደራጁ ለመከላከል ነው፤  አሊያም መምህራኑ ስለታሰሩ ሊሆን ይችላል፡፡ የተወሰኑ ተማሪዎች ወደ ትምህርት ክፍላቸው ለመሄድ ስጋት ያለባቸው እንደሆነ ሲገልጹ ወደ ትምህርትቤት አለመሄድ ደግሞ በመንግስት ላይ ተቃውሞን መግለጫ መንገድ አድርገው የወሰዱትም አሉ፡፡ ታስረው የነበሩ አራት ተማሪዎች እንደገለጹት የጸጥታ ሃይሎች ወደ ዩኒቨርስቲዎቻቸው እንዲመለሱ እንደማይፈቅዱላቸው ነግረዋቸዋል፡፡ የ6ተኛ ክፍል ተማሪ የሆነች ታዳጊ ልጅ እንደገለጸችው በትምህርት ቤቷ ከፍተኛ የተባለውን ውጤት ያስመዘገበች ቢሆንም የትምህርት ቤቱ አስተዳዳሪ በተቃውሞ ሰልፉ ስለተሳተፈች ወደ ትምህርትቤቷ እንድትመለስ ሊፈቀድላት እንደማይችል ነግረዋታል፡፡ በዚህም ምክንያት ከኢትዮጵያ ለቅቃ ለመውጣት ወስናለች፡፡

ሂውማን ራይትስ ወች ከዚህ በፊት በ2014 ዓ.ም. ተቃውሞ ተሳትፈው የነበሩ ተማሪዎች ወደ ትምህርት ቤታቸው እንዳይመለሱ መደረጉን በተመለከተ መረጃዎችን ሰብስቦ አስቀምጧል፤ ይህ አሰራር አሁን ባለው ተቃውሞ ማግስት ተግባር ላይ እየዋለ የሚገኝ ሆኖ ቀጥሏል፡፡ (ምንጭ: HRW)

Received on Tue Feb 23 2016 - 08:29:13 EST

Dehai Admin
© Copyright DEHAI-Eritrea OnLine, 1993-2013
All rights reserved