Goolgule.com: ህወሃት ራሱን በራሱ ሸንጎ አስገምግሞ የእጁን ደም ሊያጸዳ ነው

From: Berhane Habtemariam <Berhane.Habtemariam_at_gmx.de_at_dehai.org>
Date: Mon, 28 Mar 2016 21:33:14 +0200

ህወሃት ራሱን በራሱ ሸንጎ አስገምግሞ የእጁን ደም ሊያጸዳ ነው

የኮሚሽኑ ሪፖርት በኢህአዴግ ጽ/ቤት መሰራቱ ተጠቆመ
ehrc
 

ህወሃት በኦሮሚያና በአማራ ክልል በንጹሃን ዜጎች ላይ የፈጸመውን ወንጀልና ርህራሄ አልባ ግፍ ራሱ አጣርቶ፣ ራሱ አጠናክሮ፣ ራሱ በፈጠረው የሰብዓዊ መብት ኮሚሽን አማካይነት አቅርቦ፣ በራሱ ሸንጎ በማጸደቅ እጁን ከደም ሊያጸዳ ዝግጅቱን ማጠናቀቁ ይፋ መሆኑንን ተከትሎ ለሪፖርቱ ማዳመቂያ የምስል ቪዲዮዎች መዘጋጀታቸው ታወቀ

በኦሮሞና በአማራ ህዝብ ላይ የተወሰደውንና እየተወሰደ ያለውን የኃይል ርምጃ አስመልከቶ ድራማ እየተሰራ ነው ሲል የጎልጉል የአዲስ አበባ ተባባሪ ሪፖርተር የኢህአዴግ ጽ/ቤት ምንጮቹን ጠቅሶ ነው ስለ ሁኔታው የዘገበው። ህወሃት በአዋጅ ያቋቋመው የሰብዓዊ መብት ኮሚሽን መሪ ዶ/ር አዲሱ ገብረ እግዚአብሔር ቀደም ሲል በጉዳዩ ዙሪያ ሪፖርት ያቀረቡትን የመብት ተሟጋች ድርጅቶች እንደማይታመኑ ተናግረዋል።

በትግራይ ህዝብ ነጻ አውጪ ግንባር መመሪያ ሰጪነት ህወሃት በኦሮሚያና በአማራ ክልል ሰላማዊ ጥያቄ ባነሱ ኢትዮጵያዊያን ወገኖች ላይ ሲያከናውን የቆየውንና አሁንም እየተካሄደ ያለውን ገደብ የለሽ ግፍ፣ የሰብዓዊ መብት ረገጣ፣ ግድያ፣ እስር፣ አካላዊ ስቃይ፣ ማሳደድና አፈና  አስመልክቶ የሰብዓዊ መብት ተሟጋች የሆነውን ሂውማን ራይትስ ዎችን ጨምሮ ዓለም አቀፍ ተቋማትና መንግሥታት አውግዘውታል። አሁንም እያወገዙት ነው።

ህወሃት ለአገዛዙ ይጠቅመው ዘንድ በየደረጃው ካቋቋማቸው ድርጅቶች መካከል አንዱ የሆነው የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽን መሪ አዲሱ ገብረእግዚአብሔር ባለፈው ሰኞ ጋዜጣዊ መግለጫ ሰጥተው ነበር። በመግለጫቸው “ስለሰብዓዊ መብት ጥሰት ስናውራ ጥሰቱን ማን ፈጠረው” ተብሎ መሬት ተወርዶ ምርመራ መካሄድ እንደሚገባው አስገንዝበዋል። አያይዘውም በስም ባይጠሩትም ሂውማን ራይትስ ዎችን “የት ሆነው ሪፖርቱን እንደሚሰሩት ባናውቅም…” ሲሉ ህወሃትን ጥፋተኛ በማድረግ ድርጅቱ ያወጣውን ሪፖርት ሊታመን የማይችል ሲሉ ከወዲሁ ተችተዋል።

የቀድሞው የምርጫ ቦርድ ምክትል ኃላፊ የሚመሩትና “ሃቀኛ ሪፖርት ያቀረባል” የተባለው የሰብዓዊ መብት ኮሚሽን በጥቂት ቀናት ውስጥ ይፋ የሚያደርገው ሪፖርት ኢህአዴግ ጽ/ቤት እንደተጠናቀረ የጎልጉል የአዲስ አበባ ዘጋቢ አመልክቷል። እንደ ዘጋቢው፣ ሪፖርቱ ከክልል የደኅንነትና ጸጥታ መዋቀሮች የተሰበሰቡትን መረጃዎች በኮሚሽኑ ስም የሚያዘጋጀው የኢህአዴግ ጽ/ቤት፣ በኦሮሚያ የኦህዴድ ሃላፊዎች ላይ የተወሰደውን ርምጃ ያጎላል። ከህዝብ ጋር በተደረጉ “ውይይቶች” በሚል የተወሰደው የኃይል ርምጃ ከተቀሰቀሰው ረብሻ ጋር ሲነጻጸር እንደማይጋነን ህዝብ ምስክርነት እንደሰጠበትና ፈጣን ምላሽ የተወሰደበትን ጉዳይ ከጀርባ የውጪ ኃይሎች ወደ ረብሻ እንደቀየሩት አድርጎ ያሳያል።

ከዚህም በላይ የእስልምና አክራሪዎች እጅ ከጀርባ እንዳለበት በማጉላት ህወሃት የወሰደው ርምጃ “እጅግ ትዕግስት የተሞላበትና የተመጣጠነ” እንደሆነ በሪፖርቱ ይንጸባረቃል። በተጨማሪም ለማረጋጋት ተሰማራ በተባለው ሰራዊት ላይ፣ ባካባቢ ሚሊሺያዎች፣ ፖሊሶችና የሌላ ብሄር አባላት ላይ የግድያ ሙከራ መደረጉንና ቤተክርስቲያን መቃጠሉን ሪፖርቱ ህወሃት ለተጨማለቀበት ደም ማጽጃ በረኪና አድርጎ እንደሚያቀርብ ተመልክቷል።

ጠ/ሚኒስትር ሃይለማርያም “ጥፋተኞች ነን፤ ህዝብን ይቅርታ እንጠይቃለን” ማለታቸውን ተከትሎ ይፋ የሚሆነው ሪፖርት፣ ህወሃት በውክልና አገሪቱን እንዲያስተዳድሩለት የመደባቸውን ካድሬዎች ማገዱ፣ ማባረሩ፣ በህግ ለመጠየቅ መዘጋጀቱ ከወንጀሉ በስተጀርባ ሆነው ትዕዛዝ ሲሰጡ የነበሩትን የህወሃት ሹማምንቶች ነጻ እንደሚያወጣ ኦህዴድን አጋፍጦ እንደሚሰጠው ለማወቅ ተችሏል። በዚህም የፌደራል አስተዳደሩ ጣልቃ ገብቶ የማስተካከሎ ስራ መስራቱ በበጎ ጎኑ የሚቀርብ እንደሆነ ከወዲሁ ታውቋል።

አሜሪካንን ጨምሮ የተለያዩ መንግሥታት ኢህአዴግን ለወጉም ቢሆን ማብራሪያ እየጠየቁ መሆኑ፣ እንደ ሂውማን ራይትስ ዎች አይነት የሰብዓዊ መብት ተቋማት ያቀረቧቸውን ሪፖርቶች ለማጣጣል፣ ሪፖርቱ ከታሰበው ጊዜ በፊት ተጠናቅሮ እንዲወጣ ታምኖበታል። ከዚያም “በኢህአዴግ ሸንጎ ክርክር ተደርጎበት፣ ዳብሮና ተሻሽሎ ጸደቀ” ይባላል። የፖለቲካ ጨዋታ መሆኑ ቢታወቅም ለውጪው ዓለም ሚዛን ማሳቻ ይውል ዘንድ ህጋዊ ሽፋን ይሰጠዋል። ከዚያም ለፕሮፖጋንዳው ክፍሎች ተበተኖ ሥራ ላይ እንደሚውል ዘጋቢያችን አመልክቷል።

ከዚህ ጋር በተያያዘ ዓለምአቀፉ የሰብዓዊ መብት ድርጅት (ሒውማን ራይትስ ዎች) ዘገባውን ካወጣ በኋላ ለአሜሪካ መንግሥት ኃላፊዎች በዝግ ተጨማሪ ማብራሪ የተሰጣቸው መሆኑን ጎልጉል የደረሰው መረጃ ይጠቁማል። በዘገባው ላይ ያልተጠቀሱ ተጨማሪ መረጃዎችና ማብራሪያዎች ለኃላፊዎቹ የተሰጣቸው በመሆኑ ባለፉት ቀናት የሕዝብ እንደራሴዎች በተለይ የውጭ ጉዳይ መ/ቤቱን (ስቴት ዲፓርትመትን) ለኮንግረስ ዘገባ እንዲያቀርብ መጠየቃቸው ተዛማጅነት እንዳለው ይነገራል።

አስተያየት ሰጪዎች እንደሚሉት ሪፖርቱ በሚወጣበት ቀንም ሆነ አንድ ቀን ቀደም ብሎ በሁለቱም ክልሎችና በኮንሶ፣ እንዲሁም በጋምቤላ የደረሰውን ግፍና ወንጀል በማጠናከር ለዓለም አቀፍ ተቋማትና ሚዲያዎች፣ ለኤምባሲዎች፣ ለተለያዩ አገራትና በተለይም ለህዝብ በሚቻለው መንገድ ሁሉ ይፋ ማድረግ አግባብ ነው። በተለይም አስቀድሞ ለውጭ ሚዲያዎች መግለጫ በመስጠት ሪፖርቱን ራሱ ህወሃት ያዘጋጀው እንደሆነ ማስታወቅ አግባብ እንደሆነ ተገልጾዋል። ቢቻል ሪፖርቱ እየቀረበ ባለበት ወቅት የህወሃት አንጋቾችና ታማኞች እስካሀን ድረስ ያለማቋረጥ የፈጸሙትን አሰቃቂ ግፍ በማህበራዊ ገጾች ላይ አጉልቶ ማሳየት እንደሚገባ ጠቁመዋል። ባገር ቤት ያሉ የፖለቲካ ፓርቲዎች ሪፖርቱን አስመልክተው ይፋ ከመሆኑ በፊት ከወዲሁ ስራ መስራት እንደሚገባቸው ይመክራሉ።

Received on Mon Mar 28 2016 - 15:33:14 EDT

Dehai Admin
© Copyright DEHAI-Eritrea OnLine, 1993-2013
All rights reserved