Etsat.Com: የገዢው መንግስት አመራሮች ህብረተሰቡ የጦር መሳሪያ ግዥውን እንዲያቆም እየተማጸኑ ነው፡፡

From: Berhane Habtemariam <Berhane.Habtemariam_at_gmx.de_at_dehai.org>
Date: Wed, 2 Mar 2016 21:25:24 +0100

March 2, 2016

የካቲት ፳፫ (ሃያ ሦስት) ቀን ፳፻፰ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- የአማራ ክልል አመራሮች በክልሉ ጠረፋማ ከተሞች በመዘዋወር ህብረተሰቡ አጠናክሮ የያዘውን የመሳሪያ ግዥ እንዲያቆም ሲማጸኑ ተሰምተዋል፡፡

ወጣቱ አመቱን ሙሉ በተለያዩ ቦታዎች በመዘዋወር የቀን ስራ በመስራትና ከእርሻ የሚያገኙትን ገቢ በቀጥታ ለጦር መሳሪያ ግዥ ማዋላቸው የገዢውን መንግስት አመራሮችን አሳስቧቸዋል፡፡

በአሁኑ ሰዓት በመፋፋም ላይ ባለው ወቅታዊ ችግር ምክንያት በዜጎችና በመንግስት መካከል በሚታየው ፊት መዟዟር የህብረተሰቡን የልብ ትርታ ለማዳመጥ በመንቀሳቀስ ላይ ያሉት የመንግስት አመራሮች፤የጦር መሳርያ በእያንዳንዱ ወጣት እጅ መገኘቱ ለአመጽ ያነሳሳል በሚል ስጋት ላይ መሆናቸው የሚደረሱን የድምጽ መረጃዎች ያመለክታሉ፡፡

የገዥው መንግስት በጠረፋማ ወረዳዎች የሚገኙ ወጣቶች የጦር መሳሪያ እንዳይገዙ ለማስቆም የወሰነበትን ምክንያት የሚናገሩት አመራር ‹‹ወረዳዎች ጠረፋማ ከመሆናቸው ባሻገር ከኦሮሚያ ክልል ጋር የሚዋሰኑ በመሆኑ ጸረህዝቦች እና ተቀናቃኝ ኃይሎች ለፖለቲካ ትርፍ የሚጠቀሙባቸው አካባቢዎች በመሆኑ ነው፡፡››በሚል እንቅስቃሴው የጸጥታ ችግር ስጋት መሆኑን ገልጸዋል፡፡

የየአካባቢው አመራሮች በቅርበት በመሆን የህብረተሰቡን የልብ ትርታ ማዳመጥ ስላለባቸው በየጊዜው መምጣታቸውንና ህዝቡ በምን አቋም ላይ እንዳለ በመረዳት የሚከሰቱ ችግሮችን ባስቸኳይ ለመግታት እንዲያግዛቸው መሆኑን የሚናገሩት አመራር‹‹ በተለይ ወጣቱ ገንዘቡን ማዋል ያለበት ለወደፊቱ የሚጠቅመውን ለእርሻ ስራ የሚገለገልበትን እንደበሬ ያለ ንብረት መግዛት እንጅ የጦር መሳሪያ አያስፈልገውም፡፡›› በማለት ወጣቱ እየተጓዘበት ያለው መንገድ ትክክለኛ አለመሆኑን ለማስገንዘብ ጥረት ሲያደርጉ ተሰምተዋል፡፡

በአሁኑ ሰዓት በጠረፋማ ከተሞችና አካባቢዎች ከፍተኛ የመሳሪያ ሽያጭና ግዥ ግብይትን አሰራር መቆጣጠር ያልቻሉት አመራሮች ነዋሪዎችን በማግባባት በድርጊቱ ላይ የሚንቀሳቀሱ ወጣቶችን እንዲመክሩ መማጸናቸውን የአካባቢው ነዋሪዎች ‹‹የአዞእንባ›› ሲሉ ይገልጹታል፡፡

በተመሳሳይ ዜና ገዢው መንግስት በአማራ ክልል የሚገኘውን የጦርመሳሪያ ለመሰብሰብ ከፍተኛ ፍተሻና አሰሳ በማድረግ ላይ መሆኑን የጸጥታ ዘርፍ ሰዎች ተናግረዋል።

‹‹በየጊዜው መሳሪያ አምጣ በማለት ሰው እናስራለን፡፡›› የሚሉት አመራር ይህ የተደረገበት ምክንያት አሁንም ሆነ በቀጣይ መሳሪያ መያዝ ያለበት ራሱን መጠበቅ የሚፈልግ ሰው ሁሉ ሳይሆን በየአካባቢው የሚነሱ ህዝባዊ አመጾችንም ሆነ እንቅስቃሴዎች ከመንግስት ጋር በመሆን ለማብረድ የሚችል ሰው ነው ብለዋል።

በአሁኑ ሰዓት መሳሪያ የሚገዙትና የታጠቁት ለጸረ ህዝቦች ና ተቃዋሚዎች ክንድ ለመሆን የመንግስትን የመልካም አስተዳደር ጉዞ ለማስተጓጎል የሚጥሩ ወጣቶች መሆናቸውንና እነዚህ ወጣቶች ለራሳቸውም ሆነ ለሌላው ህይወት የማይጠነቀቁ በመሆናቸው ክትትል በማድረግ መሳሪያ ማስፈታቱን ሊቀጥሉበት ማሰባቸውን ገልጸዋል፡፡

አመራሩ አክለውም ‹‹ በጠረፍ ከተሞች ያሉ አርሶአደሮች ራሳቸውን መምራት የሚችሉ፣ጥሩ አንደበት ያላቸውና ተቻችለው የሚኖሩ በመሆኑ መሳሪያ አያስፈልጋቸውም ወደሚል መደምደሚያ በመደረሱ በቀጣይም አሰሳውና ፍተሻው ተጠናክሮ ይቀጥላል፡፡›› ብለዋል፡፡

*******************************************************************************

በኦህዴድ ውስጥ ሹም ሽሩ ቀጥሏል

March 2, 2016

የካቲት ፳፫ (ሃያ ሦስት) ቀን ፳፻፰ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- የኢህአዴግ አንዱ ክንፍ የሆነው የኦሮሞ ሕዝብ ዴሞክራሲያዊ ድርጅት (ኦህዴድ) ስራ አስፈጻሚ አባል የሆኑት የኦሮሚያ ከልል አስተዳደርና ፀጥታ ጉዳዮች ቢሮ ኃላፊ ከሀላፊነታቸው ተነሱ።

ምንጮቹን በመጥቀስ ሪፖርተር እንደዘገበው የክልሉ አስተዳደርና ፀጥታ ጉዳዮች ቢሮ ኃላፊ አቶ ሰለሞን ኩቹ ከሀላፊነታቸው የተነሱት ባለፈው ሳምንት መጨረሻ ኦህዴድ በኦሮሚያ ክልል እየተነሳና ዳግም እያገረሻ የሚገኘውን የፀጥታ ሁኔታ አስመልክቶ ባደረገው ግምገማ የሚጠበቅባቸውን ተግባር መወጣት አልቻሉም ተብለው ነው።

በመሆኑም በአቶ ሰሎሞን ምትክ የኦሕዴድ ሥራ አስፈጻሚና የጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም ደሳለኝ የሕዝብ አደረጃጀት አማካሪ አቶ በዙ ዋቅቤካ ደግሞ የኦሮሚያ የአስተዳደርና ፀጥታ ጉዳዮች ቢሮ ኃላፊ ሆነው እንዲሾሙ ተወስኗል፡፡

የኢሕአዴግ ሥራ አስፈጻሚና የኦሕዴድ ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ ዳባ ደበሌ በበኩላቸው በተመሳሳይ ግምገማ ከስልጣናቸው እንደተነሱና በምትካቸው የኢትዮጵያ ገቢዎችና ጉምሩክ ባለሥልጣን ዋና ዳይሬክተር አቶ በከር ሻሌ እንደተሾሙ በትናንትናው የዜና እወጃችን መዘገባችን ይታውቃል።

በኦሮሚያ ከተቀሰቀሰው አመጽ ጋር ሹም ሽሩ በስፋት እንደሚቀጥል ይጠበቃል። በሌላ በኩል አንዳንድ ከተሞች የተጀመረው የመኪና ማቆም አድማ ዛሬም ቀጥሎአል። አምቦ መስመሮችና ወሊሶ ጭር ብለው መዋላቸው ታውቋል።

በመላው ኦሮሚያ ህዝቡ የንግድና እርሻ ሥራ ግብር ገቢ ለወያኔ አናስገባም ማለት መጀመሩንም የደረሰን ዜና ያመለክታል። ገንዘባችን ለልጆቻችን መግደያ ጥይት መግዣ አይውልም የሚሉት አርሶ አደሮች፣ ሌሎች አካላትም ግብር እንዳይከፍሉ አስጠንቅቀዋል።

Received on Wed Mar 02 2016 - 15:25:26 EST

Dehai Admin
© Copyright DEHAI-Eritrea OnLine, 1993-2013
All rights reserved