Goolgule.com: “ኢያዬ ደበርሳ” – ጩኸቴን አስተላልፍ፤ የሚመራው ህዝባዊ ዓመጽ

From: Berhane Habtemariam <Berhane.Habtemariam_at_gmx.de_at_dehai.org>
Date: Mon, 21 Dec 2015 23:03:42 +0100

“መዋጮ ሲሰበሰብለት የኖረው ጦር የት አለ?” ኦቦ ቃሉ

OromoProtestsReview2015_23

አሁን በተለይ በኦሮሚያ የተቀጣጠለው ዓመጽ ከጀርባው አቀጣጣይ ኃይላት እንዳሉበት ህወሃት እየሰበከ ነው። “ጥቂት ጸረ ሰላም ሃይሎች” በማለት ብዙ አካላትን እየከሰሰም ነው። የትኛውን ኦነግ ወይም ኦነጎችን እንደሆነ ባይታወቅም እንዲያው በደፈናው “ኦነግ”ን ይከስሳል። አርበኞች ግንቦት ፯ እና አገር ቤት ያሉ ሰላማዊ ተቀናቃኞችም የአመጹ አቀጣጣይ ተደርገው ተፈርጀዋል። በተገንጣይ ስም አገር የሚገዛው የትግራይ ነጻ አውጪ ግንባር ፍረጃውን ለሚያካሂደው ጭፍጨፋ ህጋዊ ሽፋን ሊያውለው ሆን ብሎ የሚያደርገው እንደሆነ ቢታመንም “እመኑኝ” ሲሉ ኦቦ ቃሉ Oboo Qaalluu የሚሉት ሌላ ነው።

ኦቦ ቃሉ ከ25 ዓመት በላይ ኦነግን ያገለገሉና አሁን በስደት አውስትራሊያ የሚኖሩ ናቸው። በቅርቡ ውህደቱን  ይፋ ያደርጋል ተብሎ የሚገመተው የኦሮሞ ነጻነት ግንባር [ዩናይትድ] አካል ሆነው እየሰሩ ነው። እርሳቸው እንደሚሉት ኦነግ ብዙ ነው። ብዙ አመራር አለው። ብዙ ቅርንጫፍ አለው። “ዩናይትድ” የሚል ቅጽል ስም ያለው ኦነግ ማን ነው?

በአቶ ቦንሳ ተባ የሚመራው የኦሮሞ ነጻነት ግንባር [ሸሌ]፣ በአቶ ድሪባ ሆርዶፋ የሚመራው ጊዜያዊ የኦሮሞ ነጻነት ግንባር ህብረት፣ በአቶ አብደታ ኢሸኬ የሚመራው የኦሮሞ ነጻነት ታጋዮች ጥምር፣ ከእነ ጀነራል ከማል ገልቹ የተገነጠለውና በአቶ ኑሮ ደደፎ የሚመራው የኦሮሞ ነጻነት ግንባር [ቼንጅ] የሚባሉት የተለያዩ የኦነግ አካሎች የፈጠሩት ህብረት ነው። ኦነግ ከሚለው መጠሪያው ጎን [ዩናይትድ] በሚል ተቀጽላ ራሱን የሚለየው ኦነግ ኦቦ ነጋ ጃራን ሊቀመንበር፣ ጄኔራል ኃይሉ ጎንፋን ምክትል ሊቀ መንበር አድርጎ ሰይሟል። ኦቦ ቃሉ እንደሚሉት ውህደቱ በቅርቡ ይፋ ይሆናል።

ሰሞኑን “ኦነግ” በሚለው ስያሜ ከየአቅጣጫው የሚወጣው መግለጫ እንደሚያሰረዳው ኦነግ ውስጥ ያለው መከፋፈል ፈርጁ ብዙ ነው። ሕዝባዊ አልኝታነት ግን ከመግለጫና ከቃላት በላይ ሊሆን ይገባል። ኦቦ ቃሉ እንደሚሉት “መግለጫ ማንም ማውጣት ይችላል። ፍርድን ለህዝብ በመተው እስከድል ድረስ እንኳን አንድ ለመሆን አለመቻል ያሳዝናል። ልዩነትን ወደ ጎን በመተው ከመስማማት ውጪ የሚደረገው የመግለጫ ጎርፍ የማስታወቂያ ስራም ይመስላል” በማለት ጊዜው የህብረት ሊሆን እንደሚገባ ያሳስባሉ። በርግጥም ሰሞኑንን ደብዛቸው የጠፋ በርካቶች ከመግለጫቸው ጋር ለትውስታ በቅተዋል። የጠፉት ብቅ የማለታቸው ጉዳይ በቻ ሳይሆን “ታጣቂ ሃይል አለን” የሚሉትስ?

ጦር ያላቸው ክፍሎች ካሉ ከዚህ የተሻለ አጋጣሚ ስለማያገኙ ህዝብን መቀላቀል ይገባቸው እንደነበር ያመለከቱት ኦቦ ቃሉ “ይህ የተቆጣ ህዝብ፣ ምሬት የፈነቀለው ህዝብ፣ በቃኝ ያለ ህዝብ፣ ትግሉን ከዱላ በዘለለ የሚያግዘው ቢያገኝ ውጤቱ ሊፈጥን በቻለ ነበር” ባይ ናቸው። አያይዘውም “ለመሆኑ መዋጮ ሲሰበሰብለት የኖረው ጦር የት አለ?” ሲሉ ይጠይቃሉ። ብሶትና ጭቆና ባዶ እጁን ደረቱን ለጥይት ሰጥቶ አደባባይ የወጣው ህዝብ በግዳጅ፣ በፈቃደኛነት ለገንዘብ ብሎ ለህወሃት ሰዎች መሳሪያውን በመሸጥ ባዶ እጁን የቀረ ሕዝብ፤ ከወረቀት መግለጫ የዘለለ ድጋፍ እንደሚያሻው ያመላክታሉ። ኢትዮጵያን ነጻ ሊያወጡ የተነሱ ኃይሎች  መቼ ነው አንድ ወረዳ የሚቆጣጠሩት? ጥያቄው የነበረ፣ ያለና የሚኖር ነው።

የህዝባዊ አመጹ ባለቤት ማን ነው?

የኦሮሚያ ሕዝብ እንደ ሌሎች ወገኖቹ ፩ – ፭ በሚባለው አደረጃጀት እስር ቤት ሳይገባ የታሰረ ሕዝብ ነው። መዋቀሩን የሚተገብረው ደግሞ ኦህዴድ ነው። ይህ ህዝብ ሳይፈታ ሊያምጽ አይችልም። የታሰሩትን የሚፈታቸው አሳሪያቸው ብቻ ነው። ስለዚህ የራሱን ሕዝብ ጠርንፎ የነበረው ሃይል ህዝቡን ለቀቀ። ህዝብ ሲፈታ መዋቅር ፈረሰ። ኦቦ ቃሉ ይህን ማብራሪያ ካነሱ በኋላ “አብረው  መስራት ያልተስማሙ ሃይሎች የተቀናጀ አመጽን ጸንሰው፣ አዋልደውና አሳድገው ሊመሩ ይቻላቸዋል?” በማለት ይጠይቃሉ። በዚህ መነሻ አመጹ የህዝብ የመንገፍገፍ ብዛት የወለደው እንደሆነ ይናገራሉ። ብሶት ትግራይ ብቻ ሳይሆን የተበደሉ ባሉበት ቦታ ሁሉ ቀን እየጠበቀ እንደሚነሳ ይጠቁማሉ።

አሁን ኦሮሚያ ላይ የተቀጣጠለውና ህወሃትን የናጠው የህዝብ አመጽ አስመልክቶ አቶ ጃዋር መሃመድ “የኦሮሞ ህዝብ እንደዚህ ሲያመር በታሪክ አይቼ አላውቅም። ከንግዲህ የሚቀረው ህይወቱ ብቻ ነው” በማለት እንደገለጹት ኦቦ ቃሉም “በህወሃትና በኦሮሞ ሕዝብ መካከል የነበረችው የሰለለች ክር ተበጥሳለች። መልሰው እንዳይቀጥሏት ቀድሞውንም የሰለለች ነበረች። ሂደት ነው የበጠሳት። አልቆላታል።” አቶ ጃዋር ለኢሳት እንዳሉት “ደም በፈሰሰ ቁጥር ደም ይግላል። የጋለ ደም አደገኛ ነው … ካሁን በኋላ በቀድሞው መልኩ አይቅጥልም። ሁላችንም ለመሞት ዝግጁ ነን”

የፈነዳው ኦህዴድ

አንዴ በቆረኪ፣ አንዴ በካርታ፣ አንዴ በኪራይ ሰብሳቢነት፣ ወዘተ እየተነረተ፤ በግምገማ ቁም ስቅሉን እያየ ለህወሃት ልእልና የኖረው ኦህዴድ “ፈንድቷል” የሚለው አገላለጽ ተስማሚው ሆኖ ተገኝቷል። ህወሃት ኦህዴድን “ከዳኝ” ይለዋል። ለዚህም ይመስላል የፈነዳው ኦህዴድ ኦሮምያ ላይ የነበረው ውሱን አቅም ተወስዶበታል። ቀድሞውንም ቢሆን ባለሙሉ ሥልጣን ስላልነበር የህወሃት ውሳኔ ገኖ አልወጣም እንጂ ኦሮሚያ ላይ ህወሃት ኩዴታ አካሂዷል። ኦህዴድን ከጨዋታው ውጪ አድርጎታል። ሊጠግኑት ቢሉ እንኳን የሚከብድ ነው።

በቀጣይ ተሃድሶ አካሂዶ ኦህዴድ ላይ ነፍስ መዝራትና እስከ ወረዳና ቀበሌ የተዘረጋውን መዋቀር በቀላሉ አድሶ ማስቀጠል የሚቻል አይሆንም። ኦቦ ቃሉ እንደሚሉት አሁን የተጀመረው የሕዝብ እምቢተኛነት ቢቀዘቅዝ እንኳን ኦህዴድ እንደ ቀድሞው የህወሃት ታማኝ ሆኖ እንዲቀጥል ወደሚያስችለው ደረጃ አይመለስም። ታምቆ የፈነዳና ፍንዳታው ከልሉን ያናወጠ በመሆኑ መዋቀሩ ሙሉ በሙሉ ወደ ህዝባዊ ትስስር ተቀይሯል። ህወሃት እድርና እቁብ የመሳሰሉት ማህበራዊ የመጠርነፊያ መገልገያዎቹን ከስሯል። በበርካታ መመዘኛዎች ኦህዴድ ዲቃላ ሆኖ የመቆም እድሉ ከህወሃት ፍላጎት አንጻር የጠወለገ ነው። እናም ቅድመ ዝግጅት ያስፈልጋል።

ሳይቃጠል በቅጠል

“ይህ ስርዓት አደገኛ ነው። ሲወድቅ ህዝብና አገር ይዞ ይሄዳል። ግንኙነት ያስፈለጋል” በማለት ሰዎች ያሉበት ሁኔታና አቋማቸው ሳይታወቅ አቋም መያዝ እንደማይገባ አቶ ጃዋር ያሳስባሉ። እንደ እሳቸው ገልጻ ሁሉ አሁን አገሪቱ ያለችበት ሁኔታ ያሳሰባቸው ከፍሎች ያገባናል የሚሉ ወገኖች ሁሉ የፖለቲካ መሪ የመፍጠር ስራና፣ አገሪቱ ላይ ህዝብ ያስነሳውን ተቃውሞ አቅጣጫ የማስያዝ ሥራ ሊሰራ እንደሚገባ ያስገነዝባሉ።

ኦሮሚያን አስመልክተው የሚሰሩ ሚዲያዎች ከግለሰብ ማንነትና ድጋፍ ያልተላቀቁ፣ ሚዛናቸው ግለሰብን መደገፍና ማስተዋወቅ እንደሆነ የተናገሩት ኦቦ ቃሉ “ነጻና ከግለሰብ ዝና አቀንቃኝነት የተላቀቀ ሚዲያ ቢኖር ህዝብ ስለ ፖለቲካ መሪዎቹ ጥሩ ስዕል ይኖረው ነበር” ብለዋል። ማናቸውም ሚዲያዎች ሰዎችን የመታደግና የመካብ ስራ ላይ ካተኮሩ ዋና ሚናቸውን ዘንግተዋልና ሊመለሱ ይገባል። አቶ መለስ ሞተውም በሺህ የሚቆጠር ሄክታር መሬት የሚመሩት ሚዲያው እንዲገነባላቸው በተደረገው የሌለ ስብዕናቸው ሳቢያም እንደሆን መረዳት ግድ እንደሚል ተናግረዋል።

“ስለዚህ” ይላሉ አሉ ኦቦ ቃሉ “ስለዚህ ህዝብ በቃኝ ብሎ በቀሰቀሰው ማእበል ውስጥ ገብቶ የማዕበሉ ፈጣሪ ለመሆንና የማስታወቂያ ይዘት ያላቸውን መግለጫዎች ከማተም በመቀራረብ አንድ ላይ መስራት ወደሚቻለበት መንገድ ባስቸኳይ ማምራቱ አንገብጋቢ ነው” ይላሉ፡፡

“አገሪቱ እየተቸበቸበች ነው። በዚህ መልኩ ፭ ዓመት ከቀጠልን ዋጋ የለንም” በማለት አቶ ጃዋር ለሰጡት አስተያየት ኦቦ ቃሉ “የኦሮሞ መሬት ፭ ዓመት የሚቆየ ዕድሜ የለውም” የሚል ማጠናከሪያ አስተያየት ሰጥተዋል።

Received on Mon Dec 21 2015 - 17:03:43 EST

Dehai Admin
© Copyright DEHAI-Eritrea OnLine, 1993-2013
All rights reserved